የታዋቂው አፕል ኩባንያ ምርት የሆነው አይፎን ለገበያ መቅረብ የጀመረበትን አስረኛ አመት እያከበረ ሲሆን፣ ባለፉት አስር አመታት ከ1 ቢሊዮን በላይ የተለያዩ አይነት የአይፎን ስማርት ስልኮችን ለተጠቃሚዎች መሸጣቸው ተነግሯል፡፡ ከአለማችን ፈርቀዳጅ የስማርት ስልኮች አንዱ የሆነው አይፎን ላለፉት አመታት ከፍተኛ ተወዳጅነት ይዞ በስፋት ሲሸጥ መቆየቱን የዘገበው ቴክ ኒውስ፣ አምራቹ ኩባንያ አፕልም ከትርፋማ ኩባንያዎች አንዱ ሆኖ መዝለቁን ገልጧል፡፡
በየሳምንቱ 500 ሚሊዮን ያህል አለማቀፍ ደንበኞች የአፕልን የአፕሊኬሽን ስቶር እንደሚጎበኙ የተነገረ ሲሆን፣ ባለፉት 10 አመታት ከ180 ቢሊዮን በላይ የአፕል አፕሊኬሽኖች ዳውንሎድ መደረጋቸው ተጠቅሷል፡፡
አፕል በመጪው መስከረም ወር አዲሱን አይፎን 8 ስማርት ስልኩን ለገበያ ያበቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፣ የመሸጫ ዋጋው ከ1 ሺህ ዶላር በላይ ይሆናል መባሉንና ይህም ከአይፎን ስልኮች የመሸጫ ዋጋ ከፍተኛው እንደሚሆን አስረድቷል፡፡
Published in
ከአለም ዙሪያ