Print this page
Sunday, 16 July 2017 00:00

በአዲስ አበባ መስተዳድር ከ1.4 ቢሊዮን ብር በላይ ባክኗል ተባለ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(1 Vote)

“ብክነትና ምዝበራ በፈጸሙት ላይ ህጋዊ እርምጃ ይወሰዳል”

በ2008 የበጀት ዓመት በአዲስ አበባ መስተዳድር፣ከ1.4 ቢሊዮን ብር በላይ ያለ አግባብ መባከኑን የከተማዋ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ባለፈው ረቡዕ ለአዲስ አበባ ም/ቤት ባቀረበው ሪፖርት አስታውቋል፡፡
ሪፖርቱን ለም/ቤቱ ያቀረቡት የከተማ አስተዳደሩ ዋና ኦዲተር ወ/ሮ ፅጌወይን ካሣ፤ ብክነትና ምዝበራ በፈፀሙ አካላት ላይ ከፀረ ሙስና እና ከፖሊስ ጋር በመተባበር እርምጃ እንደሚወሰድ ገልፀዋል፡፡
በመስተዳድሩ የ2008 የበጀት ዓመት በወቅቱ ያልተሰበሰበ 500 ሚሊዮን ብር የመንግሥትና የህዝብ ገንዘብ እንዳለ በሪፖርቱ የተጠቆመ ሲሆን በወቅቱ ያልተወራረደ 200 ሚሊዮን ብር፣ ለማን እንደተከፈለ ማስረጃ የሌለው ወይም የማይታወቅ 257 ሚሊዮን ብር እንዲሁም አዋጅና መመሪያን ሳይከተል ለውሎ አበልና ለደመወዝ የተከፈለ ከ353 ሚሊዮን ብር በላይ በኦዲት መገኘቱ ተመልክቷል፡፡
የመንግሥት የግዥ መመሪያን ተከትሎ ያለመስራት፣ በመመሪያና በህግ ከተፈቀደው በላይ የውሎ አበል ክፍያን መፈፀም ለበጀቱ ብክነት ዋነኛ ምክንያት ነው ብሏል - ሪፖርቱ፡፡
የም/ቤቱ አፈ ጉባኤ ዶ/ር ታቦር ገ/መድህን በበኩላቸው፤ የኦዲት ግኝት ያለባቸው ተቋማት ተለይተው የእርምት እርምጃ እንደሚወሰድ ለም/ቤቱ አባላት ተናግረዋል፡፡






Read 4773 times