Monday, 07 August 2017 00:00

የቀድሞ የማላዊ መሪ፤ በ100 ሚሊዮኖች ዶላር ሙስና ይፈለጋሉ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

  ማላዊን ለአራት አመታት ያስተዳደሩት የቀድሞ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጆይስ ባንዳ፣ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር ተመዝብሮበታል በተባለ የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ የእስር ትዕዛዝ የወጣባቸው ሲሆን በአሜሪካ የሚገኙት ባንዳ ግን “ወንጀሉን አልፈጸምኩም፣ ወደ አገሬ ተመልሼ ንጽህናዬን አረጋግጣለሁ” ብለዋል፡፡
በእሳቸው የስልጣን ዘመን ተሰራ ከተባለው ሙስና ጋር በተያያዘ ፕሬዚዳንቷን ጨምሮ 70 የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት፣ ነጋዴዎችና የመንግስት ሰራተኞች መከሰሳቸውን የዘገበው አልጀዚራ፤ በ2014 በምርጫ መሸነፋቸውን ተከትሎ ወደ አሜሪካ በማቅናት፣ በአንድ የልማት ተቋም ውስጥ በመስራት ላይ የሚገኙት ጆይስ ባንዳ ግን፤ በስልጣን ዘመኔ እንዲህ ያለ አስጸያፊ ተግባር አልፈጸምኩም ሲሉ ውንጀላውን ማጣጣላቸውን አመልክቷል፡፡
በአሁነ ወቅት ለስራ ጉዳይ ባመሩበት ደቡብ አፍሪካ የሚገኙት ጆይስ ባንዳ፤ የአገሪቱ ፖሊስ የእስር ማዘዣ እንዳወጣባቸው መስማታቸውን ተከትሎ፣ ለሮይተርስ በስልክ በሰጡት መግለጫ፣ በስልጣን ዘመናቸው ሙስናን በትጋት የታገሉና የመጀመሪያውን የጸረ ሙስና ኮሚሽን ያቋቋሙ፣ የመጀመሪያዋ የአገሪቱ መሪ እሳቸው መሆናቸውን በመጥቀስ፣ ወደ አገሬ ተመልሼ የሚመጣውን ሁሉ ለመጋፈጥ ዝግጁ ነኝ፤ ምንም የሚያስጠይቀኝ ነገር ስላልሰራሁ የሚያስፈራኝ ነገር የለም ብለዋል፡፡
የቀድሞዋ የማላዊ ፕሬዚዳንት ጆይስ ባንዳ፣ በደቡብ አፍሪካ እያከናወኑት የሚገኙትን የበጎ ምግባር ተልዕኮ እንዳጠናቀቁ፣ ወደ አገራቸው በመመለስ፣ የፍርድ ቤት ምርመራ ሂደቱን እንደሚከታተሉ ይጠበቃል ተብሏል፡፡

Read 1381 times