Monday, 07 August 2017 00:00

500 ቱርካውያን በመፈንቅለ መንግስቱ ተከስሰው ፍ/ ቤት ቀረቡ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

     ፍርድ ቤቱ፣ በወህኒ ቤት ቅጽር ግቢ ውስጥ የተቋቋመ ነው

      ባለፈው አመት በተሞከረውና በከሸፈው የቱርክ መፈንቅለ መንግስት ሴራ፣ እጃቸው አለበት ተብለው የተከሰሱ 500 ያህል ቱርካውያን ባለፈው ማክሰኞ በአገሪቱ እጅግ ግዙፉ እንደሆነ በሚነገርለትና በወህኒ ቤት ውስጥ በተቋቋመው ፍርድ ቤት መቅረባቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ተከሳሾቹ የአገሪቱን ፕሬዚዳንት ጠይብ ኤርዶጋንን ለመግደልና የከሸፈው መፈንቅለ መንግስት ሙከራ አካል የነበረውንና ከአንካራ አቅራቢያ ከሚገኝ የአየር ሃይል ጣቢያ የተነሱ የጦር ጀቶች የአገሪቱን ፓርላማ የደበደቡበትን ጥቃት በማስተባበርና በማቀናጀት ወንጀል ተጠርጥረው መታሰራቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ከተከሳሾቹ መካከል የቀድሞው የአገሪቱ የአየር ሃይል ዋና አዛዥ አኪን ኦዝቱክር እንደሚገኙበት የጠቆመው ዘገባው፤ አገር በመክዳትና በሽብርተኝነት የተከሰሱት ግለሰቡ፣ የቀረቡባቸውን ክሶች ተቃውመው መከራከራቸውን ገልጧል፡፡
ከ1 ሺህ በላይ በሚሆኑ ወታደሮች ታጅቦ በጥብቅ ክትትል የተከናወነው ችሎት፣ ወደተከናወነበት ግዙፍ ፍርድ ቤት የቀረቡት ተከሳሾች፣ የተከሰሱባቸው የወንጀል አይነቶች የተለያዩ ቢሆኑም፣ አብዛኞቹ ጥፋተኛ ሆነው ከተገኙ በእድሜ ልክ እስራት ሊቀጡ እንደሚችሉ መነገሩን ዘገባው አመልክቷል፡፡
የተከሳሾቹን ጉዳይ በመመርመር ላይ የሚገኘው ፍርድ ቤቱ፤ በአገሪቱ ግዙፉ እንደሆነና 1 ሺህ 558 ሰዎችን ማስተናገድ የሚችል እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ ሲኒካን ውስጥ በሚገኝ ትልቅ ወህኒ ቤት ቅጽር ግቢ ውስጥ የሚገኘው ፍርድ ቤቱ፣ ከመፈንቅለ መንግስት ጋር የተያያዙ ክሶችን ለማስተናገድ ብቻ ታስቦ በቱርክ መንግስት መቋቋሙንም አስረድቷል፡፡
የጠይብ ኤርዶጋን መንግስት ከከሸፈው መፈንቅለ መንግስት ጋር በተያያዘ ለእስር የዳረጋቸው ዜጎቹ ቁጥር ከ50 ሺህ በላይ እንደሚሆን የጠቆመው ዘገባው፤ የጅምላ እስር እና ከስራ የማባረር እርምጃው፣የአውሮፓ ህብረትን ጨምሮ ከበርካታ አካላት ተቃውሞ እንዳጋጠመውም አስታውሷል፡፡

Read 1948 times