Friday, 11 August 2017 00:00

በ7 ኪ.ግ ወርቅ የተሰራው ኮምፒውተር፣ በ1 ሚ. ዶላር ለገበያ ቀርቧል

Written by 
Rate this item
(4 votes)

 ፕራይም ኮምፒውተር የተባለውና ተቀማጭነቱ በስዊዘርላንድ የሆነው ኩባንያ፤ ከደምበኞቹ የሚቀርቡለትን የተቀናጡ ምርቶች ጥያቄ  ለመመለስ በማቀድ ያመረተውን በ18 ካራት ወርቅ የተሰራ አዲስ አይነት ዴስክቶፕ ኮምፒውተር ባሳለፍነው ሳምንት በ1 ሚሊዮን ዶላር፣ በተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ ለገበያ ማቅረቡ ተዘግቧል፡፡
ሰባት ኪሎ ግራም በሚመዝን ንጹህ ወርቅ የተሰራው ይህ በአይነቱ ልዩ የሆነ ኮምፒውተር፤አምስት ቴራ ባይት ሃርድ ድራይቭ እንዳለው የዘገበው አይፒቲኔት፣ በተለያዩ ኦፐሬቲንግ ሲስተሞች እንደሚሰራና ከአምስት አመት ዋስትና ጋር ለሽያጭ መቅረቡንም አመልክቷል፡፡
ኩባንያው ፕራይም ጎልድ የሚል ስያሜ የሰጠውንና በተወሰነ መጠን አምርቶ ለገበያ ያቀረበውን ይህን ኮምፒውተር፤ በቀጣይም ባልተለመደ ሁኔታ አሻሽሎ ለማዘመን እቅድ መያዙን የጠቆመው ዘገባው፤ ከእነዚህ ማሻሻያዎች መካከልም የኮምፒውተሩን የማብሪያና ማጥፊያ ቁልፍ፣ እጅግ ውድ ዋጋ ባለው የከበረ ድንጋይ መስራት እንደሚገኝበት አስረድቷል፡፡
በዱባይ ከዚህ ቀደምም ከወርቅ የተሰሩ የአፕልና የብላክቤሪ ምርቶች ለገበያ ቀርበው እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ በጁሜራህ የሚገኘው እና በአገሪቱ እጅግ ዝነኛው እንደሆነ በሚነገርለት ቡርጂ አል አረብ ሆቴል፣ ደምበኞቹ በቆይታቸው የሚጠቀሙበትን ባለ24 ካራት ወርቅ አይፖድ፣ በነጻ እንደሚሰጥም አመልክቷል፡፡

Read 3042 times Last modified on Saturday, 05 August 2017 12:28