Saturday, 02 September 2017 11:50

ሶማሊያ 50 ስደተኛ ኢትዮጵያውያንን በግዳጅ ወደ ሀገራቸው መለሰች

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(5 votes)

16 ያህሉ ህፃናት ናቸው ተብሏል
   የሶማሊያ መንግስት ወደ መካከለኛው ምስራቅ በስደት ጉዞ ላይ የነበሩ 16 ህፃናትን ጨምሮ 50 ኢትዮጵያውያንን በቁጥጥር ስር አውላ፣ በግዳጅ ወደ ሀገራቸው የመለሰች ሲሆን በሌላ በኩል፤ 260 ሶማሊያውያንና ኢትዮጵያውያን፣ በሊቢያ በተደራጁ የወንጀለኛ ቡድኖች እጅ ወድቀው እየተሰቃዩ መሆኑ ተዘግቧል፡፡
በሶማሊያ በቀጥጥር ስር የዋሉት ስደተኛ ኢትዮጵያውያኑ በፑንትላንድ አድርገው፣ የሜድትራኒያን በባህር ተሻግረው፣ ወደ መካከለኛው ምስራቅ ሀገራት ለስራ ፍለጋ ያመሩ የነበሩ መሆናቸውን አለማቀፉ የስደተኞች ተቋም (IOM) አስታውቋል፡፡
በሶማሊያ የፀጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ስር ውለው፣ በግድ ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ከተደረጉት ኢትዮጵያውያን 5ቱ ሴቶች፣ 29 ወንዶች እና 16ቱ ህፃናት መሆናቸው ታውቋል፡፡ በሌላ በኩል 260 ሶማሊያውያንና ኢትዮጵያውያን፤ በሊቢያ በተደራጁ የወንጀለኛ ቡድኖች እጅ ወድቀው ድብደባና የተለያዩ የማሰቃየት ተግባራት ሲፈፀምባቸው የሚያሳይ የቪዲዮ በማህበራዊ ሚዲያዎች መለቀቁን ተከትሎ አለማቀፉ የስደተኞች ተቋም፤ ቪዲዮው ከማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ እንዲነሳ ቢጠይቅም ከፌስ ቡክ አስተዳዳሪች አዎንታዊ ምላሽ አለማግኘቱን አስታውቋል፡፡
ስደተኞቹ በወንጀል ቡድኖቹ እጅ ከወደቁ በኋላ እያንዳንዳቸው 8ሺህ ዶላር ያህል ከየቤተሰቦቻቸው እንዲያስልኩ በመጠየቅ ድብደባና እንግልቱ እየተፈፀመባቸው መሆኑን የመረጃ ምንጮች ዘግበዋል፡፡
በተለይ የስቃይ ምስሎቹ በማህበራዊ ሚዲያዎች መተላለፋቸውን የተቃወመው ተቋሙ፤ “ለቤተሰቦቻቸው ተጨማሪ ስቃይ ይፈጥራል የሚል ስጋት እንዳለው ገልጿል፡፡
በአሁን ወቅት በኢትዮጵያ ላለው የታዳጊዎችና ወጣቶች ስደት፣ ከኢኮኖሚ ችግር በተጨማሪ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የተከሰተው ድርቅ ምክንያት መሆኑን አለማቀፉ የስደተኞች ተቋም አስታወቋል፡፡
የሳውዲ አረቢያ መንግስት “ህገ ወጦች ሀገሬን ለቅቃችሁ ውጡልኝ” ሲል ያስቀመጠው ጠቅላላ የ150 ቀናት የጊዜ ገደብ መጠናቀቁን የጠቀሰው አይኦኤም፤ ኢትዮጵያውያንን ወደ ሀገራቸው ለመመለስና ለማቋቋም 30 ሚሊዮን ዶላር ያህል በጀት ያስፈልጋል ብሏል፡፡    


Read 2831 times