Saturday, 02 September 2017 11:51

አስራ ሦስት ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በኬንያ ታስረዋል

Written by 
Rate this item
(5 votes)

የኬንያ ፖሊስ በህገ ወጥ መንገድ ወደ አገሪቱ ገብተዋል ያላቸውን 13 ኢትዮጵያውያን ባለፈው ረቡዕ ምሽት በመዲናዋ ናይሮቢ በቁጥጥር ስር ማዋሉንና ለፍርድ ለማቅረብ በምርመራ ላይ እንደሚገኝ ዥንዋ ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
በህገወጥ መንገድ ድንበር አቋርጠው ወደ ኬንያ ገብተዋል የተባሉት ኢትዮጵያውያኑ፣ በመዲናዋ ናይሮቢ በተከራዩት አንድ ቤት ውስጥ ለቀናት ተደብቀው እንደቆዩ የጠቆመው የከተማዋ ፖሊስ፤ ወደ ደቡብ አፍሪካ ሊያሸጋግራቸው የተስማማን አንድ ህገወጥ የሰዎች አዘዋዋሪ በመጠበቅ ላይ ሳሉ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን አመልክቷል፡፡
በእስር ላይ የሚገኙት ኢትዮጵያውያን ሁሉም ወንዶች ሲሆኑ በተለያዩ ወንጀሎች ተከስሰው ቅጣት እንደሚጣልባቸውና ወደ አገራቸው እንደሚመለሱ ያስታወቀው ፖሊስ፣ ህገወጥ የሰዎች አዘዋዋሪውንና በወንጀሉ ተሳትፈዋል ያላቸውን ሁለት ሴቶች በቁጥጥር ስር ለማዋል ዘመቻ እንደጀመረም ገልጿል፡፡
ወደ ታንዛኒያ እና ደቡብ አፍሪካ ለመሻገር በማሰብ፣ በህገወጥ መንገድ ወደ ኬንያ ገብተው የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩን የጠቆመው ፖሊስ፤ በየአመቱ እስከ 100 የሚደርሱ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በኬንያ ፖሊስ ቁጥጥር ስር እንደሚውሉም አመልክቷል፡፡

Read 3078 times