Print this page
Sunday, 03 September 2017 00:00

በኢትዮጵያ 15 ሚ. ቡና አምራች ገበሬዎች ለአደጋ ተጋልጠዋል

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(10 votes)

   በኢትዮጵያ 15 ሚሊዮን ያህል የቡና አምራች ገበሬዎች ህይወት፤ በዓለም ሙቀት መጨመር ሳቢያ ለአደጋ መጋለጡን አልጀዚራ ዘግቧል፡፡
በአፍሪካ በቡና አምራችነት ቀዳሚ የሆነችውና በዓለም በ5ኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው ኢትዮጵያ፤ በአሁን ወቅት 15 ሚሊዮን ያህል የቡና አምራች ገበሬዎቿ ከሙቀት መጨመር ጋር በተያያዘ፣ የቡና እርሻቸው እየተጎዳና ምርታቸው እያሽቆለቆለ መሆኑ ተመልክቷል፡፡
አልጀዚራ፤ በደቡብ ኢትዮጵያ፣ ሲዳማ አካባቢ ያነጋገራቸው ቡና አምራች አቶ ከበደ ገርማሙ “በበጋ ወቅት የፀሐይ ኃይሉ የበረታ በመሆኑ፣ ሙቀቱ ለቡና ተክል ተስማሚ አልሆነም” ብለዋል። በዚህ ምክንያት የቡና ምርታቸው በእጅጉ ማሽቆልቆሉን ተናግረዋል፡፡
የቡና ተክል ከ15 እስከ 26 ዲግሪ ሴሊሺየስ ብቻ ሙቀት የሚፈልግ ቢሆንም በአሁን ወቅት በቡና አምራች አካባቢዎች ያለው ሙቀት ከ26 ዲግሪ ሴሊሺየስ በላይ መሆኑ እንዳሳሰባቸው አርሶ አደሮቹ አስታውቀዋል፡፡ የቡና ገበሬዎች ይህን ሙቀት ለመቋቋምና የቡና ተክላቸውን ህይወት ለማቆየት የእንሰት ተክልን በየቡና እርሻቸው መሃል በመትከል፣ ሙቀቱን ለመቋቋም ጥረት እያደረጉ መሆኑ ተገልጿል፡፡
በቅርቡ ይፋ የተደረገ አንድ አለማቀፍ ጥናት፤ በኢትዮጵያ ቡና አምራች ከነበሩ የሀገሪቱ አካባቢዎች መካከል 60 በመቶ ያህሉ በአየር ፀባይ ለውጥ ምክንያት፣ በክፍለ ዘመኑ መጨረሻ ቡና ማምረት እንደማይችሉ ጠቁሟል፡፡  

Read 3501 times