Sunday, 03 September 2017 00:00

ማሳደግ እንጂ ማስረገዝ አይከብድም (የጋሞኛ ተረት)

Written by 
Rate this item
(11 votes)

    ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ በጣም አባቱን የሚፈራ ልዑል ነበር፡፡ በፍርሃቱ ምክንያት የሠራውን ሥራ ሁሉ ለንጉሡ ከመናገር ይቆጠባል፡፡ ከሁሉም በላይ ልጅየውን፣ ልዑሉን የሚያስደነግጠው አባትየው ምንም ነገር ቢሰማ አይደነቅም፡፡ ስለዚህ፤ አንድ አዲስ ነገር ሲያቀርብለት፤
“በርታ፤ ገና ይቀርሃል” ይላል፡፡
ልዑሉም፤
“ምን ባደርግ ነው አባቴ ደስ ብሎትና ፍንድቅድቅ ብሎ፤ ‹ይሄ ነው የእኔ ልጅ! እንኳን ወለድኩህ! ዕውነተኛው የአባትህ ልጅ አንተ ነህ!!› የሚለኝ?” እያለ ወደ መኝታው ይሄዳል፡፡
አንድ ቀን ልዑሉ የአባቱን ጦር ይዞ ወራሪ ጉረቤት ሊዋጋ ከቤተመንግሥት ይወጣል፡፡ ጦርነቱ ድንበር ላይ የሚካሄድ ነው፡፡
ንጉሡ ልጅ፤ ጦር “እየመራ ወደ ጠረፍ መሄዱን ሰምቶ፣ ኖሮ ወደ ጦር ሜዳው” በድብቅ ሄደ፡፡
ጦርነቱ ተጀመረ፡፡ ከሁለቱም ወገን በርካታ ሰው እንደ ቅጠል ይረግፍ ጀመር፡፡ ልዑሉ አልተበገረም። “ወደፊት እንግፋ፤ ማፈግፈግ የለም!” እያለ እራሱ ከፊት ከፊት እየተወነጨፈ የሚያስደንቅ ጀግንነት አሳየ፡፡ ጠዋት የተጀመረው ጦርነት፣ ረፋዱ ላይ ጋብ ያለ ይመስልና ደግሞ እኩለ-ቀን አካባቢ እንደገና ትርምስምሱ ይወጣል፡፡ ውጊያው ይፋፋማል! ከሁለቱም ወገን ሰው ይረፈረፋል! በመጨረሻ ግን በርካታ ወገን ይለቅበት እንጂ ልዑሉ በአሸናፊነት ተወጣው! ድል የእሱ ሆነ! የማረካቸውን የጠላት ወታደሮች ይዞ፣ ወደ ቤተ-መንግሥቱ ተመለሰ፡፡
ከጥቂት ሰዓት በኋላ ንጉሡ፤ ልዑሉን ወደ ዙፋኑ እንዲቀርብ አስጠራው፡፡ ልዑሉ መጣ፡፡ የጦር ልብሱን፣ ጥሩሩን እንደለበሰ ነው የቀረበው! የጀግንነት ስሜቱ ፊቱ ላይ ይነበባል፡፡
ንጉሡ፡-
ልጄ ሆይ! ገድልህን አይቻለሁ፡፡ አንተ ሳታየኝ ጦር ሜዳ ድረስ መጥቼ ሁኔታውን ሁሉ ተከታትያለሁ። ወራሪውን በአኩሪ ደረጃ ድል መትተሃል! ለመሆኑ ለምን ሳትነግረኝ ወደ ጦር ሜዳ ሄድክ?
ልዑሉ፡-
አባቴ ሆይ! እኔ ልጅህ በራሴ የምኮራ መሆኔን እንድታውቅ እፈልጋለሁ፡፡ አንተ በቤተ መንግሥት ወግ አሳድገኸኛል፡፡ ፈረስ ጉግሥ፣ ጦር ውርወራ፣የሠራዊት አመራር፣ ዳኝነት፣ የጠላትን መረጃ ማግኘት፣ ካሰፈለገ መጥለፍ ሁሉ አስተምረኸኛል፡፡ የተማርኩትን በሥራ ላይ ማዋል፤ የእኔ ፋንታ ነው፡፡ በዚያ ረገድ አላሳፈርኩህም ብዬ አምናለሁ፡፡
ንጉሥ፡-
ዕውነት ነው ልጄ፣ ከቶም አላሳፈርከኝም
ልዑል፡-
እንግዲያው አባቴ፤ “በርታ፤ ገና ይቀርሃል” አትለኝም ማለት ነው፤ አይደደል?
ንጉሥ፡-
ልጄ ሆይ! አሁንም ገና ይቀርሃል!
ልዑል፡-
ደሞ ምን ቀረኝ አባቴ?
ንጉሥ፡-
አትቸኩል፡፡ እነግርሃለሁ፡፡ በጠላት ወገን ብዙ ወታደር አልቋል፡፡ ያም ሆኖ ካንተም ወገን ብዙ ሰው ወድቋል፡፡ መሆን አልነበረበትም፡፡
ልዑል፡-
ስለዚህ ምን ማድረግ ነበረብኝ?
ንጉሥ፡-
“ማፈግፈግ! ማፈግፈግ ማወቅ አለብህ፡፡ ላወቀበት፣ ማፈግፈግ ከማጥቃት አንድ ነው፡፡ የምትለቅለት ሥፍራ የወጥመድህ ዋና አካል ነው፡፡ የአሸናፊነትና የመደላደል ስሜት ሲሰማው፡- አንተ ስስ-ብልቱን አገኘህ ማለት ነው፡፡ ያኔ ሠራዊትህን ሳታስጨርስ ዒላማ ታደርገዋለህ፤ በቀላሉ ትደመስሰዋለህ! የማፈግፈግ ስልት ማወቅ ምን ጊዜም የማይለይህ ጥበብ ይሁን! ከሁሉም በላይ ግን ድሉ የአገርህ ድል መሆኑን ተማር! ብርታትን ሁሉ አብዝቶ ይለግሥህ ልጄ! በሚቀጥለው ጊዜ እንደምትክሰኝ ተስፋ አለኝ! ያኔ ጣፋጭ ድል ታገኛለህ!” አለና አሰናበተው፡፡
* * *
ሀገራችን ጦርነት፣ ግጭት፣ ደም መፋሰስና ቅራኔ ተለይቷት አያውቅም፡፡ በመሣፍንት  ያየችውን፣ በነገሥታት እየደገመች፣ የነገሥታቱን ታሪክ በወታደር በትጥቅ ትግል እያጎላች፤ ብዙ ዘመን ተጉዛለች፡፡ ይህን ዚቅ እንገላገለው ዘንድ ሰላምን ያልተመኘንበት ጊዜ አልነበረም፡፡ ሆኖም መልኩን እየቀያየረ ሰላም መደፍረሱ አልቀረም፡፡ ከሥጋት፣ ከፍርሃት፣ ከጥርጣሬ፣ ከተስፋ-ማጣት ያልተላቀቀ ማህበረሰብ፤ ሰላም አለው ለማለት አያስደፍርም፡፡ የሀገራችንን ነገር በቅንነት ላስተዋለ አደፍራሹ ብዙ ነው፡፡ የውስጥም የውጪም ሰላም-ነሺ በርካታ ነው፡፡ ቅራኔን በአግባቡ መፍታት እስካልቻልን ድረስ፤ እኛም የማደፍረሱ ሂደት አካል መሆናችን አይቀሬ ነው፡፡ ኢ-ፍትሐዊ ሁኔታ ሰላም ይነሳል፡፡ ኢ-ሰብአዊ ሁኔታ ሰላም ይነሳል፡፡ ምዝበራ ሰላም ይነሳል፡፡ የአገር ገንዘብ እየዘረፉ ማሸሽ ሰላም ይነሳል። በትልቅ በትንሹ ጠብ ያለሽ-በዳቦ የሚል ብሶተኛ መኖር፣ ሰላም ነሺ የሆነውን ያህል፤ እሱ አደብ-እንዲገዛ ለማድረግ የሚሰነዘረው ምላሽም ሰላም ነሺ ከሆነ፤ ተያይዞ ገደል ነው፡፡ ከአንዱ ሰላም-ማጣት ወደ ሌላ ሰላም ማጣት መሸጋገር ከድጡ ወደማጡ መዝቀጥ ነው! አገርን በሆደ-ሰፊነት የሚመራ፣ በብልህነት የተቃኘ፣ “ትዕግሥት ፍርሃት አይደለም” የማይል፤ መልካም አስተዳደር ሙሉ ትርጉም የገባው አመራር ያስፈልገናል! ቆም ብሎ የሚያይ፤
“ጀግናው ጉተናዬ፤
ሎጋው ተዋጊዬ፤
ጥቃት ቢሰነዝር፣ ምን ድሉ ቢቀናው
ማፈግፈግ ካልቻለ፣ ገና ነው ፈተናው፡፡
የሚለው ግጥም በግልፅ የተጤነው፤ የማይደናበር፣ አስተዋይ የአገር ሰው ያስፈልገናል፡፡ የአገር ሽማግሌ ጠፍቶብናል፡፡ እርቅ ያለ አስታራቂ፣ ሰላም ያለ ሰላማዊ ሰው እንደማይመጣ ተዘንግቶናል! ነገር ማነሳሳት፣ ቅራኔን ማሾር፣ አለመግባባትን ማቀጣጠል፣ መፍትሄ ይሁንም አይሁን በጅልነት “አረረም መረረም ማ’በሬን ተወጣሁ” ማለትን፣ “እሳት ሳይኖር ጭስ አይታይም” የሚለውን ብሂል ዘንግቶ፣ ምንም እንዳልተፈጠረ አድርጎ ነገርን መናቅን፣አለመገንዘብ አደገኛ ነው፡፡ ከቶውንም ይሁን ይሁን ተብሎ የተወሰነ ነገር፣ ነገ ፍሬ አለው የለውም ብሎ አለመጠየቅ፤ “ማሳደግ እንጂ ማስረገዝ አይከብድም” የሚለውን የጋሞኛ ተረት ያስታውሰናልና ጠንቀቅ እንበል!!  

Read 7929 times