Saturday, 02 September 2017 12:16

በኬንያ ፌስታል መጠቀምና ማምረት 4 አመት እስርና 40 ሺህ ዶላር ያስቀጣል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

   ብክለትን ለመቀነስ የወጣው ህግ 176 ፋብሪካዎችን ያዘጋል፣ 60 ሺህ ሰራተኞችን ያፈናቅላል

        የኬንያ መንግስት፤ የፕላስቲክ ከረጢት ወይም ፌስታል ባመረተ ወይም በተጠቀመ ላይ እስከ 4 አመት እስር እና 40 ሺህ ዶላር የገንዘብ ቅጣት የሚጥልና በአለማችን በመስኩ እጅግ ጥብቅ የተባለ ህግ አውጥቷል፡፡
በኬንያ ከሰኞ ጀምሮ የፕላስቲክ ከረጢት ይዞ የተገኘ የአገሪቱ ዜጋ፣ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውሎ ተገቢው ቅጣት እንደሚጣልበት የጠቆመው ዘገባው፤ የፕላስቲክ ከረጢቶችን የሚያመርቱ ፋብሪካዎችም ቁጥጥር እንደሚደረግባቸው አመልክቷል፡፡
የፕላስቲክ ምርቶች በአካባቢ ብክለት ረገድ የሚፈጥሩትን ተጽዕኖ ለመቀነስ ታስቦ የወጣው ይህ እጅግ ጥብቅ ህግ፤ ከቀጣዩ ሰኞ ጀምሮ በስራ ላይ እንደሚውል የዘገበው ዘ ጋርዲያን፣ በአገሪቱ የፕላስቲክ ከረጢቶች በየቦታው እየተጣሉ ከፍተኛ ብክለት እየፈጠሩ እንዳሉም አመልክቷል፡፡
የፕላስቲክ ከረጢቶች ለመበስበስ እስከ 1000 አመታት የሚደርስ ጊዜ እንደሚፈጁ የገለጸው ዘገባው፤ እንስሳትም ያገለገሉ የፕላስቲክ ከረጢቶችን በመመገብ ለጤና ችግር እንደሚጋለጡና በመዲናዋ ናይሮቢ በሚገኙ የከብት ማረጃ ቄራዎች ከአንድ ከብት ሆድ ዕቃ ውስጥ እስከ 20 የሚደርሱ ያገለገሉ የፕላስቲክ ከረጢቶች እንደሚገኙ ጠቁሟል፡፡
የፕላስቲክ ከረጢት ምርቶችን ወደ ውጭ አገራት በመላክ፣ከአካባቢው አገራት በቀዳሚነት የምትሰለፈው ኬንያ፣ የአካባቢ ብክለትን ለመቀነስ በሚል ያወጣቺው ይህ ህግ፣ በአገሪቱ የሚገኙ 176 ፋብሪካዎችን የሚያስዘጋና ከ60 ሺህ በላይ ዜጎችን ከስራ የሚያፈናቅል ነው በሚል የአገሪቱ የአምራች ኩባንያዎች ማህበር  ክፉኛ ተችቶታል፡፡
ቻይና፣ ፈረንሳይ፣ ሩዋንዳና ጣሊያንን ጨምሮ የተለያዩ 40 የአለማችን አገራት፣ የፕላስቲክ ከረጢቶችን ምርት በከፊል ወይም ሙሉ ለሙሉ የሚከልክሉ ተመሳሳይ ህጎችን አውጥተው በስራ ላይ ማዋላቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

Read 1375 times