Print this page
Saturday, 02 September 2017 12:26

በ“ሆሄ” የሥነ - ፅሑፍ ሽልማት - እነማን ተሸለሙ?

Written by 
Rate this item
(3 votes)

  በረጅም ልብወለድ- አዳም ረታ (“የስንብት ቀለማት”)
በሥነ ግጥም- አበረ አያሌው (“ፍርድና እርድ”)
 በልጆች መፅሐፍ - አስረስ በቀለ (“የቤዛ ቡችላ”)
ኢስትዌስት ኢንተርቴይንመትና ኤቨንት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ለመጀመሪያ ጊዜ ያዘጋጁት “ሆሄ” የሥነ ፅሑፍ ሽልማት፣ባለፈው ሰኞ ምሽት በብሔራዊ ትያትር ባካሄደው ሥነሥርዓት በየዘርፉ ተወዳድረው ያሸነፉትን  ሸልሟል፡፡ ዋናዎቹ የውድድር ዘርፎች ረጅም ልብወለድ፣ሥነግጥምና የልጆች መጻሃፍት ሲሆኑ ከሐምሌ 2008 እስከ ሐምሌ 2009 ዓ.ም ተፅፈው ለንባብ የበቁ መፅሐፍት በውድድሩ መካተታቸው  ታውቋል፡፡ ለእያንዳንዱ ዘርፍ ሶስት ሶስት ዳኞች ተመድበው ምርጫና ምዘናው መካሄዱም ተጠቁሟል፡፡ 80 በመቶ በዳኞች ምዘና ፣20 በመቶ ደግሞ በአንባቢያን ምርጫ መሰረት፣  አሸናፊዎቹ እንደተለዩ ተነግሯል፡፡
በረጅም ልቦለድ ዘርፍ ለውድድር ከቀረቡት ሥራዎች መካከል የዶ/ር ዓለማየሁ ዋሴ “ዝጎራ”፣ የአዳም ተረታ “የስንብት ቀለማት”፣ የሰብለ ወንጌል ፀጋ “መፅሀፉ”፣ የያለው አክሊሉ “ወሰብሳቤ” እና የብርሀኑ አለባቸው “የሱፍ አበባ” ለመጨረሻው ዙር ያለፉ ሲሆን  የደራሲ አዳም ረታ “የስንብት ቀለማት፣ አሸናፊ ሆኗል፡፡ ደራሲው በሃገር ውስጥ ስለሌለም፣ተወካዩ፣ ከደራሲ ሳህለ ስላሴ ብርሀነ ማሪያም እጅ ሽልማቱን ተቀብሏል፡፡
በግጥም መፅሀፍ ዘርፍ ለውድድር ከቀረቡት ሥራዎች ውስጥ የኤፍሬም ስዩም “ኑ ግድግዳ እናፍርስ”፣ የትዕግስት ማሞ “የጎደሉ ገፆች”፣ የአበረ አያሌው “ፍርድና እርድ”፣ የዶክተር በድሉ “ተስፋ ክትባት” እና የበላይ በቀለ ወያ “እንቅልፍና ሴት” የግጥም መፅሀፍት ለመጨረሻው ዙር ያለፉ ሲሆን  የአበረ አያሌው “ፍርድና እርድ” አሸናፊ ሆኖ ከገጣሚ፣ ባለቅኔና ፀሀፌ ተውኔት አያልነህ ሙላቱ እጅ ሽልማቱን  ወስዷል፡፡
በልጆች መፅሐፍ ዘርፍ ከቀረቡት ሶስት መፅሐፎች መካከል የኮሜዲያን አሥረስ በቀለ “የቤዛ ቡችላ” የተሰኘ መፅሐፍ አሸናፊ ሆኗል፡፡ ለመጨረሻው ዙር ካለፉት ሶስት የልጆች መፅሐፍት ሁለቱ የአሥረስ በቀለ ናቸው፡፡ ኮሚዲያን አሥረስ በቀለ ሽልማቱን ከተቀበለ በኋላ ባደረገው አጭር ንግግር፤ “እኔ ሁሌም ተስፋ ሳልቆርጥ ስለምሰራ ለዚህ በቅቻለሁ፤ ዛሬ ሆሄ የሽልማት ድርጅት ከሥነ-ፅሁፍ ጋር በይፋ ድሮኛል” ሲል ደስታውን ገልጧል፡፡ ኮሜዲያኑ አስከትሎም፤ “ዛሬ አበባ ተስፋዬ በህይወት ኖረው፣ ይህንን ክብር ቢያዩልኝ  ምን ያህል በታደልኩ” ሲል በቁጭት ስሜት ተናግሯል፡፡  
የ”ሆሄ” ሌሎች ተሸላሚዎች  
የላቀ አስተዋፅኦ ያበረከተ የሚዲያ ተቋም -
ሸገር ኤፍኤም 102.1 ሬዲዮ
በረጅም ዘመን የትምህርት ማስፋፋት የላቀ ባለውለታ- አቶ ማሞ ከበደ ሽንቁጥ
ለአይነ ስውራን መፅሀፍትን ተደራሽ በማድረግ የላቀ አስተዋፅኦ ያበረከተ- “አዲስ ህይወት ለአይነ ስውራን ማዕከል”
በረጅም ዘመን ጋዜጠኝነትና ስነ-ፅሁፍን በትረካ ለህዝብ በማድረስ - ጋዜጠኛ ደጀኔ ጥላሁን
በረጅም ዘመን የኃያሲነትና ስነ-ፅሁፍ ሥራ የላቀ አስተዋፅኦ በማበርከት- ኃያሲና ደራሲ አስፋው ዳምጤ
በህይወት ዘመን የስነ-ፅሁፍ ሽልማት- አለቃ አካለወልድ ክፍሌ (“መፅሀፈ ሰዋሰው ወግዕዝ”)

Read 2062 times
Administrator

Latest from Administrator