Sunday, 03 September 2017 00:00

ጄኬ ሮውሊንግ፤ በ95 ሚ. ዶላር የዓመቱ ከፍተኛ ተከፋይ ደራሲ ሆናለች

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 ጌም ኦፍ ትሮንስ በተመልካቾች ብዛት ክብረ ወሰን አስመዝግቧል

       የሃሪ ፖተር ተከታታይ መጽሃፍት ደራሲ የሆነቺው እንግሊዛዊቷ ጄኬ ሮውሊንግ፣ የ2017 የአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ ደራሲ መሆኗን የዘገበው ኢኮኖሚክ ታይምስ፣ ደራሲዋ ከሰኔ ወር 2016 አንስቶ በነበሩት 12 ወራት ከመጽሃፍቷ ሽያጭ በድምሩ 95 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷን አስታውቋል፡፡
የመጀመሪያውን የሃሪ ፖተር መጽሃፍ ለንባብ ያበቃችበትን 20ኛ አመት ክብረ በዓል በቅርቡ ያከበረቺው ደራሲዋ፣ መጽሃፍቶቿ ከፍተኛ ተወዳጅነትን በማግኘት በገፍ መቸብቸባቸውን ቢቀጥሉም፣ የአለማችን ቁጥር አንድ ከፍተኛ ተከፋይ ደራሲ ስትሆን ግን ይህ ከአስር ዓመታት በኋላ የመጀመሪያ ጊዜዋ መሆኑን አመልክቷል፡፡
ጄምስ ፓተርሰን በ87 ሚሊዮን ዶላር ሁለተኛ፣ ጄፍ ኬኒ በ21 ሚሊዮን ዶላር፣ ዳን ብራውን በ20 ሚሊዮን ዶላር፣ ስቴፈን ኪንግ በ15 ሚሊዮን ዶላር አመታዊ የህትመትና የኤሌክትሮኒክስ መጽሃፍት ሽያጭ ገቢ፣ በቅደም ተከተላቸው እስከ አምስተኛ ያለውን ደረጃ የያዙ የአለማችን ድንቅ ደራሲያን መሆናቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ተወዳጅ ሆኖ የዘለቀውና ሰባተኛው ሲዝን ላይ የደረሰው ጌም ኦፍ ትሮንስ ተከታታይ ፊልም ከሰሞኑ በታሪኩ ከፍተኛውን የተመልካች ቁጥር ማግኘቱ ተዘግቧል፡፡ የጌም ኦፍ ትሮንስ የሲዝን ሰባት ማጠናቀቂያ በ12.1 ሚሊዮን ተመልካቾች በቀጥታ፣ በ16.5 ሚሊዮን ተመልካቾች ደግሞ ከቀጥታ ስርጭት በኋላ መታየቱን የዘገበው ፎርብስ መጽሄት፤ከዚህ ቀደም በቀጥታ የተከታተሉት ተመልካቾች ከፍተኛው ቁጥር 10.1 ሚሊዮን እንደነበር አስታውሷል፡፡


Read 3029 times