Monday, 04 September 2017 00:00

ሰሜን ኮርያ ገና ብዙ ባለስቲክ ሚሳኤሎችን አስወነጭፋለሁ አለች

Written by 
Rate this item
(7 votes)

እሳትና ውሃ ቀርቦላታል፤ እጇን ወዳሻት መስደድ የእሷ ምርጫ ነው- ዶናልድ ትራምፕ

       ባለፈው ማክሰኞ ባልተጠበቀ ሁኔታ ባለስቲክ ሚሳኤል ወደ ጃፓን በማስወንጨፍ አለምን በድንጋጤ ክው ያደረገቺው ሰሜን ኮርያ፣ “ይህ እኮ በፓሲፊክ አካባቢ የማደርገው ወታደራዊ ዘመቻ ጅማሬ ነው፤ ገና ብዙ ሚሳኤሎችን ወደ አካባቢው አስወነጭፋለሁ” ስትል በይፋ ተናግራለች፡፡
የሰሜን ኮርያው ፕሬዚዳንት ኪም ጆንግ ኡን፤ ሚሳኤሉን ያስወነጨፍነው አሜሪካና ደቡብ ኮርያ እያደረጉት ለሚገኘው ወታደራዊ ልምምድ ምላሽ ለመስጠት ነው፣ የአገሬ ጦር በፓሲፊክ አካባቢ የሚያካሂደውና የአሜሪካ ግዛት የሆነቺውን ጉኣም ለማጥቃት ያለመው ቀጣይ ወታደራዊ ዘመቻ ጅማሬ ነው ሲሉ በይፋ ማስታወቃቸውን ኬሲኤንኤ የተባለው የአገሪቱ መንግስት መገናኛ ብዙሃን ዘግቧል፡፡
“ያስወነጨፍነው ሚሳኤል አሪፍ መነቃቂያ ነው፤ ከፍተኛ እርካታ ተሰምቶኛል” ሲሉ በይፋ የተናገሩት ፕሬዚዳንቱ፤ በቀጣይም ተመሳሳይ በርከት ያሉ ሚሳኤሎችን ወደ አካባቢው እንዲያስወነጭፍ ለአገሪቱ የጦር ሃይል ትዕዛዝ ማስተላለፋቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
ሰሜን ኮርያ ከሚሳኤል ሙከራዋ እንድትታቀብ በተባበሩት መንግስታት ድርጅትና በአገራት መንግስታት ተደጋጋሚ ጫና ቢደረግባትም ባለፉት ወራት በተጠናከረ ሁኔታ የሚሳኤል ሙከራ ስታደርግ መቆየቷን ያስታወሰው ዘገባው፤ የማክሰኞው የሚሳኤል ማስወንጨፍ ድርጊት ግን ብዙዎችን ያስደነገጠ ነው ብሏል፡፡
ከፒንግያንግ አቅራቢያ ከሚገኝ ጣቢያ ወደ ጃፓን አቅጣጫ የተወነጨፈው ይህ ሚሳኤል፤ 2ሺህ 700 ኪሎ ሜትሮች ያህል በመጓዝ በሰሜናዊ ጃፓን በሚገኘው ሆካይዶ ደሴት ላይ ቢያርፍም በነዋሪዎች ላይ ምንም አይነት ጉዳት አለማድረሱን ያስታወሰው ዘገባው፣ ድርጊቱ የጃፓንን መንግስት በከፍተኛ ሁኔታ ማስደንገጡንና ይህን ተከትሎ፣ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በሰጡት መግለጫ፤ ድርጊቱ ያልተጠበቀ፣ አጅግ አደገኛና አውዳሚ ስጋት ነው ሲሉ ሰሜን ኮርያን መኮነናቸውን አመልክቷል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ የሰሜን ኮርያ ድርጊት ለጃፓንና ለአካባቢው አገራት ብቻ ሳይሆን ለሁሉም የተመድ አባል አገራት ከፍተኛ ስጋት ነው በሚል ድርጊቱን በይፋ ያወገዘው ሲሆን ሩስያና ቻይና ግን በአካባቢው ውጥረት እንዲነግስ ያደረገው የአሜሪካ ወታደራዊ ልምምድ ነው ሲሉ አሜሪካን ኮንነዋል፡፡
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው፤ ድርጊቱ ሰሜን ኮርያ ለጎረቤት አገራት ያላትን ጥላቻ ያሳየችበት ነው፣ ከአሁን በኋላ እሳትና ውሃ ቀርቦላታል፤ እጇን ወዳሻት መስደድ የእሷ ምርጫ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡

Read 7215 times