Saturday, 07 October 2017 14:25

የ5 ባለሃብቶችና የሥራ ሃላፊዎች የሙስና ክስ በአቃቤ ህግ ተቋርጧል

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(15 votes)

    የአምስት ባለሃብቶችና የስራ ሃላፊዎች የሙስና ክስ ጉዳይ በጠቅላይ አቃቤ ህግ እንዲቋረጥ ተደርጓል፡፡ ከ50 በላይ የሚሆኑ ባለስልጣናት፣ ባለሃብቶችና ግለሠቦች ከሁለት ወራት በፊት በሙስና ተጠርጥረው በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን የሁለት ባለሃብቶችን ጉዳይ ጨምሮ የ5 ተጠርጣሪዎች ክስ ሠሞኑን ተቋርጧል፡፡ በትላንትናው እለት በቀድሞ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ዛይድ ወ/ገብርኤል የክስ መዝገብ ውስጥ ተካተው ጉዳያቸው በፍ/ቤት ሲታይ ከነበሩት መካከል የሣትኮን ኮንስትራክሽን ባለቤት አቶ ሳሙኤል ተክላይ፣ የሀይዚአይ አይ ኮንስትራክሽን ባለቤት አቶ ዛኪር አህመድ እንዲሁም በሳትኮን ኮንስትራክሽን የፋይናንስ መምሪያ ሃላፊ የነበሩት አቶ ፍሠሃ ታደሰ ክስ በአቃቤ ህግ ተቋርጧል፡፡
የሣትኮም ባለቤት አቶ ሳሙኤል ተክላይና የፋይናንስ ሃላፊው አቶ ፍስሃ ታደሰ አስቀድሞም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ሣይውሉ ቀርተው፤ የእስር ትዕዛዝ ወጥቶባቸው የነበረ ሲሆን የሀይዚ አይአይ ኮንስትራክሽን ባለቤት አቶ ዛኪር አህመድ ግን በፖሊስ ጣቢያ ታስረው የሚገኙ መሆኑ ተጠቅሷል። በዚህም መሰረት አቶ ዛኪር አህመድ ከፖሊስ ጣቢያ የሚለቀቁ ሲሆን ሁለቱ ተከሳሾች ባሉበት ክሳቸው እንዲቋረጥ ተደርጓል፡፡
በተመሣሣይ በሣምንቱ መጀመሪያ ላይ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን ኮሚኒኬሽን ሃላፊ አቶ ሣምሶን ወንድሙና ሌላው የመስሪያ ቤቱ ባልደረባ አቶ በቀለ ባልቻ ክስ በአቃቤ ህግ መቋረጡን ይታወሳል፡፡
አቃቢ ህግ የአቶ ሣምሶንን ክስ ያቋረጠው “በተጠርጣሪው ላይ ክስ መመስረት ስላልተቻለ ነው” ብሏል፡፡ በአቶ በቀለ ባልቻ ላይ ደግሞ ክስ መመስረት ስላላስፈለገ ምርመራውን ያቋረጠ መሆኑን በመግለፅ ከእስር መለቀቃቸውን አስረድቷል፡፡


Read 5751 times