Sunday, 22 October 2017 00:00

የአሜሪካ 400 ቀዳሚ ባለጸጎች ይፋ ተደረጉ

Written by 
Rate this item
(3 votes)

  • የማይክሮ ሶፍት መሥራች ቢል ጌትስ፣ ለ24ኛ ጊዜ በ1ኛነት ይመራሉ
    • ትራምፕ ከፍተኛውን ኪሳራ ሲያስተናግዱ፣ ዙክበርግ ከፍተኛውን ጭማሪ አስመዝግቧል

     ታዋቂው ፎርብስ መጽሔት፣ በአገረ አሜሪካ የሚኖሩ የአመቱ 400 ቀዳሚ ባለጸጎችን ዝርዝር ከሰሞኑ ይፋ ያደረገ ሲሆን ከአምናው ሃብታቸው የ8 ቢሊዮን ዶላር ጭማሪ በማስመዝገብ፣ የ89 ቢሊዮን ዶላር ባለጸጋ ለመሆን የበቁት የማይክሮሶፍቱ መስራች ቢል ጌትስ ዘንድሮም እንደለመዱት ለ24ኛ ጊዜ በአንደኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል፡፡
በአምናው ሃብታቸው ላይ የ14.5 ቢሊዮን ዶላር ጭማሪ ሃብት አፍርተው፣ ዘንድሮ የ81.5 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት ባለቤት የሆኑት የአማዞኑ መስራች ጄፍ ቤዞስ የሁለተኛነት ደረጃን ሲይዙ፣ ዋረን በፌ ሦስተኛነቱን ተቆናጥጠዋል፡፡
በሃብቱ ላይ በ12 ወራት የ15.5 ቢሊዮን ዶላር ጭማሪ ያከለው የፌስቡኩ መስራች ማርክ ዙክበርግ በአመቱ ከፍተኛውን የሃብት ጭማሪ ያስመዘገበ የአሜሪካ ቢሊየነር መሆኑን ያስታወቀው የፎርብስ መረጃ፤ በደረጃ ሰንጠረዡ ላይም በአራተኛነት መቀመጡን አስረድቷል፡፡ ከአሜሪካ ባለጸጎች መካከል 289 ያህሉ ሃብታቸው ከአምናው ዘንድሮ ጭማሪ ያሳየ ሲሆን 51 ባለጸጎች በአንጻሩ ሃብታቸው መቀነሱን የጠቆመው ፎርብስ፤ከሁሉም ሃብታቸው በከፍተኛ ደረጃ የቀነሰው የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ  ናቸው ብሏል፡፡ ባለፉት 12 ወራት ውስጥ 600 ሚሊዮን ዶላር ማጣታቸውንም ዘግቧል - መጽሔቱ፡፡ 

Read 3170 times