Sunday, 29 October 2017 00:00

ኢ/ር መላኩ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ም/ቤት አዲስ ፕሬዚዳንት ሆነው ተመረጡ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(4 votes)

የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ለቀጣዩ ሁለት ዓመታት ምክር ቤቱን የሚመራ የፕሬዚዳንት፣ የምክትል ፕሬዚዳንትና የቦርድ አባላት ምርጫ ያካሄደ ሲሆን የአማራ ክልል የንግድና የዘርፍ ማህበራት ም/ቤትን የወከሉት ኢ/ር መላኩ እዘዘው፤ 87 ድምፅ በማግኘት በፕሬዚዳንትነት ተመርጠዋል፡፡
ም/ቤቱ 8ኛ መደበኛ ጉባኤውን ትላንት በሂልተን ሆቴል ያካሄደ ሲሆን፣ በአገር አቀፍ ደረጃ ካሉት 18 የንግድ ም/ቤት አባላት መካከል 17ቱ ለምርጫው እጩዎችን አቅርበው ነበር፡፡ ኢ/ር መላኩ ቀደም ሲል የጎንደር ከተማ የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤትን ለአራት አመት በፕሬዚዳንትነት የመሩ ሲሆን በአሁን ሰዓት ደግሞ የክልሉ የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሆነው እያገለገሉ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡
ኢ/ር መላኩ ከ17 ዓመት በፊት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቴክኖሎጂ ፋካልቲ በኤሌክትሪካል ኢኒጂነሪንግ በመጀመሪያ ዲግሪ የተመረቁ ሲሆን ከስድስት ዓመት በፊት ደግሞ በማስተር ኦፍ ቢዝነስ አድሚኒስቴሬሽን ኤንድ ስፔሻላይዜሽን ፕሮጀክት ማኔጅመንት ሁለተኛ ዲግሪያቸውን አግኝተዋል፡፡
ኢ/ር መላኩ ለሁለት አስርተ ዓመታት ገደማ በንግድ ስራና ክህሎት ላይ ያሳለፉ ሲሆን በኤሌክትሪካል ምህንድስናና በኮምፒዩተር ሳይንስ፣ በኮምፒዩተር ስልጠና፣ ጥገናና ሽያጭም ለተወሰኑ ጊዜያት ሰርተዋል፡፡ ኢ/ር መላኩ ከዚያ ቀጥለው በተለያየዩ የስራ መስኮች በጎንደር ከተማ የሚገኝ “ቤተ - መላኩ” የተሰኘ የሪል ስቴት፣ የተሽከርካሪ ማሰልጠኛና የትራንስፖርት ንግድ ባለቤት ናቸው፡፡
የኦሮሚያ የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ፈይሳ አራርሳ የኢ/ር መላኩ ከፍተኛ ተፎካካሪ የነበሩ ቢሆንም በ12 ነጥብ ተበልጠው ሳያሸንፉ ቀርተዋል፡፡
በምክትል ፕሬዚዳንትነት የተመረጡት የትግራዩ አቶ አስፋ ገ/ስላሴ ሲሆኑ ም/ቤቱ በአጠቃላይ 1 ፕሬዚዳንት 1 ም/ፕሬዚዳንት እና 9 የቦርድ አባላት በድምሩ 11 አመራሮችን መርጧል፡፡ የዘንድሮውም ምርጫ ፍፁም ሰላማዊና መጠናቀቁን የሚናገሩት ታዛቢዎች አድንቀቅታል፡፡

Read 2401 times