Saturday, 09 December 2017 13:29

ቅማንት አማራ ነው ወይ? አማራ ማን ነው?

Written by  ጸጋየ ሞላ (ከጎንደር ዩኒቨርሲቲ)
Rate this item
(3 votes)


             “አማራነት ስነ-ልቦናዊ ስሜት እንጅ የዘርና የቋንቋ ጉዳይ ብቻ እንዳልሆነ አምነናል፡፡ ሙስሊሙም ክርስቲያኑም፣ ቅማንቱም፣ አገውም…የራሱን ልዩ
የሚያደርገውን ባህል እንደያዘ፣ በትልቁ ሲሰፋ የአማራ ማንነትን ይዞ ኢትዮጵያዊነትን ያፈካል፡፡ ደግሞ በ21ኛው ክፍለ-ዘመን ዘር የሚባል ባዮሎጂ የለም፡፡
አማራ፣ ኦሮሞ፣ ጉራጌ… የሚል ዘረ-መል በህክምና አታገኝም፡፡…”
          ጸጋየ ሞላ (ከጎንደር ዩኒቨርሲቲ)

     ቅድመ-ነገር
የአማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት ጋዜጠኛና የማህበራዊ ሚዲያ ንቁ ተሳታፊ የሆነው የሺሀሳብ አበራ “እንቧለሌ” የሚል መጽሃፍ አሳትሞ ባለፈው ሳምንት ገበያ ላይ ውሏል፡፡ ጋዜጠኛው የአማራ ብሄርተኝነት አቀንቃኝ፣ ብዙ ተከታይ ያለው፣ የመንግስት ጋዜጠኛና ወጣት በመሆኑ የተነሳ በእሱ በኩል የአማራ ወጣቶችን የፖለቲካ አረዳድ፣ አቋምና አፈታት ለማወቅ እንደሚረዳኝ በማመን “እንቧለሌ”ን ተሽቀዳድሜ አነበብኳት፡፡ በጠቅላላ አነጋገር ሙሉ በሙሉ ፖለቲካዊ ጉዳዮችን የያዘች የወግ መጽሃፍ ናት ማለት እችላለሁ፡፡ በመጽሃፉ ብዙ ገጾችና ታሪኮች ላይ የአማራ ብሄርተኝነትን ትዳስሳለች፡፡ ትኩረቴን የሳበኝና ለዚህች አጭር ጽሁፍ መነሻ የሆነኝን ታሪክ ያገኘሁት ቅማንት እንደ ክሪሚያ የተመሰለችበት የወግ ክፍል ነው፡፡ የዚህ ጽሁፌ ዓላማ በመጽሃፉ ላይ ሙሉ ዳሰሳ ማቅረብ አይደለም፡፡ የቅማንትን ነጠላ-ታሪክና የእንቧለሌን የብሄር ብያኔ መነሻ በማድረግ፣ አማራነት ምንድነው? የሚል ውይይት ፣ክርክርና ሙግት መክፈት ነው፡፡ ቅማንት በመጀመሪያ በአማራ ክልል ምክር ቤት ይሁንታና በኋላ በፌዴሬሽን ምክር ቤት አስፈጻሚነት በተደረገ ህዝበ- ውሳኔ፣ አንድ ቀበሌ ተጨምሮለት “ብሄረሰብ” መሆኑ ታውቆለት፣ የራሱን አስተዳደር እንዲመሰርት ተፈቅዷል፡፡
መግቢያ
የማህበራዊ ሳይንስ ጽንሰ-ሃሳቦች ተበይነው ያለቁ አይደሉም፡፡ ብሄርተኝነት በስተቀር አይደለም፡፡ ከስም አጠራሩ ጀምሮ በምን ማለትነቱ ላይ ስምምነት የለም፡፡ ስምምነት የለም ማለት አንድ ዓይነት አረዳድ የለም ማለት እንጅ ብሄርተኝነት አይታወቅም፤ እንግዳ ነገር ነው ማለት ከቶ አይደለም፡፡ የአማራ ብሄርተኝነት ካለፉት ሁለት ዓመታት ጀምሮ በመቀንቀን ላይ ነው፡፡
ብሄርተኝነት ቀለመ - ብዙ መሆኑ፣ የአማራ ብሄርተኝነት በተለይ ከኢትዮጵያዊነት ጋር ካለው ተመሳስሎሽ ጋር ተደምሮ፣ የአማራ ብሄርተኝነት ምንድን ነው? ለሚለው ጥያቄ የተቆረጠ መልስ መስጠትን አስቸጋሪ አድርጎታል። የአማራ ብሄርተኝነትን መነሻ፣ የመሄጃ መንገዶችና መድረሻውን ለይቶ ለማወቅ በቅድሚያ የብሄርተኝነቱን ወርድና ስፋት የሚወስነውን ምን ማለትነቱን መበየን አስፈላጊ ይሆናል፡፡ ብሄር ምንድነው? ብሄር የአንድ ሰው ተፈጥሯዊ ዘር ነው የሚሉ (Primoridialist Theory)፤ የስልጣን መያዣ ኤሊት-ሰራሽ የፖለቲካ መሳሪያ ነው የሚሉ (Instrumentalist View) እና የጊዜና የሁኔታዎች ሂደት ውጤት የሆነ ማህበረሰባዊ ስሪት ነው የሚሉ(Socially Constructed) የዘርፉ ምሁራን የከረመ ሙግት አላቸው፡፡ እነዚህ ብሄርን ማን ሰራው የሚል ጥያቄን በመመለስ የብሄርን ምን መሆን የመመለስ ሙከራ የሚመዝዛቸው ክሮች ናቸው፡፡ አንድ ማህበረሰብ ብሄር የሚሆነው ምን ምን ቅድመ-ሁኔታዎችን ሲያሟላ ነው? ብሄርን የሚያቋቁሙ መስፈርቶች ምንድን ናቸው? የሚለውን ስንጠይቅ ቋንቋ፣ ባህል፣ ስነ - ልቦና፣ መልክዓ - ምድር ወዘተ ሆነው እናገኛለን፡፡ ብሄርን የሚያቋቁሙ ቅድመ-ሁኔታዎች ሆነው የተቀመጡት መስፈርቶች በብሄር ውስጥ ያላቸው ድርሻ (የሚያቀብሉት አበርክቶ) ምን ያህል እንደሆነ በህግም ሆነ በአካዳሚያዊ (የምርምር) ጽሁፎች ተወስኖ አይገኝም፡፡ እነዚህ መስፈርቶች በጣምራነት (Commulative) መሟላት ያለባቸው ወይም በአማራጭነት ሊተካኩ የሚችሉ (Optional) ስለመሆናቸውም እንዲሁ፡፡ እነዚህ መስፈርቶች ‹ሰብጀክቲቭ› የሆነውን የብሄር ማንነት፣ ‹ኦብጀክቲቭ› የሆነ መስፈሪያ የማበጀት ሙከራዎች ናቸው፡፡
ከዚህ በቀር ለሁሉም ብሄሮች በተመሳሳይ ድርሻና ተጽዕኖ (ማዋጣት) ሊያገለግሉ አይችሉም። የአማራ ብሄርተኝነት በእነዚህ መስፈርቶች ተሰፍሮ የሚያልፍ መሆኑ የማያከራክር ቢሆንም የመስፈርቶቹ ድርሻና ተጽዕኖ ምን ያህል እንደሆነ መገምገም የብሄርተኝነቱን ተፈጥሮና መጠነ-ዙሪያ ለመቀንበብ ያገለግላል፡፡
 የቅማንት ነገር
 የቅማንትን የብሄር ጥያቄ በመጀመሪያ ወደ አደባባይ ይዘው የወጡት አቶ ነጋ ጌጤ፣ ቅዳሜ ሃምሌ 12 ቀን 2006 ዓ.ም ለወጣው አዲስ አድማስ ጋዜጣ በሰጡት ቃለ-መጠይቅ፤ ‹‹የቅማንት ብሄረሰብ ቀደምት ከሚባሉት ውስጥ አንዱ ነው። መገለጫው በእኛ በቅማንቶች አባት፣ እሚታ፣ አያት፣ ቅድመ - አያት - ­ቅማንት - ምንዥላት - እንጃላት ብለን 7ኛ ቤት ድረስ ይሄዳል፡፡ 6ኛው ዙር ምንዥላት የሚባለው አሁን ጠፍቷል፡፡ አሁን ያለው የመጨረሻው ቅማንት ነው፡፡ እነዚህ ከአባት ተጀምሮ ወደ ላይ የሚጠሩት የዘር ተዋረዶች ናቸው፡፡ …ኖህ ሶስት ልጆች አሏቸው - ሴም፣ ያፌት፣ ካም ይባላሉ፡፡ አፍሪካውያን የካም ልጆች ናቸው፡፡ ከዚህ መሃል የእኛን ዘር የምናወጣው ከከነአን ልጆች ነው፡፡ አራዲዮን- አደረኪን ወለደ። አደረስኪ ሶስት ሚስቶችን አገቡ፡፡ አንደኛዋ ሚስታቸው አንዛኩና ትባላለች፡፡ ከአንዛኩና ቅማንት….ይወለዳሉ፡፡…›› ይላሉ፡፡ ይህ የአቶ ነጋ ጌጤ ትርክት፣ ብሄር በቀጥታ የዘር ቆጠራ እንደሆነ የሚነግረን ነው፡፡ የአቶ ነጋ ጌጤ የዘር ቆጠራ የሚያነሱትን የብሄር ማንነት ይገባናል ጥያቄ የሚደግፍ አይሆንም፡፡ በህገ-መንግስቱ ዘር የብሄር ማንነትን የሚያስገኝ መስፈርት ሆኖ አልተደነገገም፡፡ ብሄርን በዘር የወደ ኋላ ቆጠራ ለማግኘት የሚደረግ ጉዞ ማረፊያው የአማራና የኦሮሞ ብሄሮችን ከአንድ ዘር የተገኙ ናቸው ወይም የሰው ሁሉ ዘር አንድ ነው ወይም በተለይ አማራ የሚባል ብሄር የለም የሚል ይሆናል፡፡ ስለሆነም እገሌ እንቶኔን ወለደ ዓይነት የብሄርተኝነት ትርክት ብሄርተኝነትን የሚንድና ትርጉም የማይሰጥ ነው፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ባለ በደምና በአጥንት በተዋሃደ ህዝብ መካከል ዘርን ተከትሎ አንዱን ከሌላው ለመለየት  መሞከር የሚቻል አይደለም፡፡ ብሄርተኝነትንም ከፖለቲካ ርዕዮትነት አውርዶ የለየለት ዘረኝነት ያደርገዋል። አንድ ማህበረሰብ ብሄር ለመሆን የተለየ ዘሩን እንዲቆጥር የሚያስገድድ የህግም ሆነ የማህበራዊ ስምምነት በሌለበት ሁኔታ፣ አቶ ነጋ ጌጤ፣ የቅማንትን ራሱን የቻለ የተለየ ብሄር መሆኑን ለማስረዳት እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ ዘር የመቁጠራቸው ተጠየቅ ግልጽ አይደለም፡፡ ባህል፣ ቋንቋ፣ ስነ-ልቦ­ ና፣ መልክዓ ምድር …የሚሉት ቅድመ-ሁኔታዎች፣ ቅማንትን ከጎንደሬው የማይለዩት ስለሆነ ልዩነትን ፍለጋ ይመስላል፡፡ ቅማንት በአሁኑ ጊዜ የብሄር እውቅና ተሰጥቶት የራሱን አስተዳደር አቋቁሟል፡፡ እውቅና የተሰጠው ግን በየትኞቹ መስፈርቶች ተመዝኖና ምን ምን አሟልቶ በመገኘቱ እንደሆነ ግልጽ አይደለም፡፡ በአማራና በቅማንት መካከል ያለውን አንድ መሆንና ያው ራስነት ስናይ፣ የቅማንት ብሄርተኝነት ልሂቅ-ሰራሽ የፖለቲካ መሳሪያ እንጅ መሬት ያለ የሚጨበጥ ማህበረሰባዊ መሰረት ያለው አይመስልም፡፡ የቅማንት ማንነት መነሻው ምንም ቢሆን መድረሻው ራስን በራስ የማስተዳደርና እውቅና የማግኘት፣ እንደ አገውነት፣ አርጎባነት…ወዘተ እስከሆነ ድረስ የሚፈጥረው የኀልዮትም ይሁን የተግባር መፋለስ አይኖርም፡፡ ይህን ነጥብ በዝርዝር ከማየታችን በፊት ብሄርተኝነት ይልቁንም አማራነት በ”እንቧለሌ” የተገለጠበትን ዓይነት እንመልከት፡፡
“አማራነት ስነ-ልቦናዊ ስሜት እንጅ የዘርና የቋንቋ ጉዳይ ብቻ እንዳልሆነ አምነናል፡፡ ሙስሊሙም ክርስቲያኑም፣ ቅማንቱም፣ አገውም…የራሱን ልዩ የሚያደርገውን ባህል እንደያዘ፣ በትልቁ ሲሰፋ የአማራ ማንነትን ይዞ ኢትዮጵያዊነትን ያፈካል፡፡ ደግሞ በ21ኛው ክፍለ-ዘመን ዘር የሚባል ባዮሎጂ የለም፡፡ አማራ፣ ኦሮሞ፣ ጉራጌ…የሚል ዘረ-መል በህክምና አታገኝም፡፡…ብሄር በፖለቲካ የሚፈጠር ማህበራዊ ውህደት ያለው የነገድ መጠሪያ ነው፡፡ …ብሄር የሚባለውም የደም ጉዳይ ሳይሆን የጋራ ስነ-ልቦና የሚፈጥረው የህዝብ ጉባዔ ነው”› (ገጽ 79)
 ይህን የምትለን በእንቧለሌ የፖለቲካዊ ወጎች መጽሃፍ ላይ የቅማንት አማራ ሆና የተሳለችውና በሙያዋ የስነ-ማህበረሰብና የታሪክ ተመራማሪና አዝማሪ መሆኗን የምትነግረን ዶ/ር አበበች ደሴ ናት። ”እኔ እንደ ቅማንት ከአማራው የሚነጠል ማንነት የለኝም፡፡…አንጓው ቢለያይም ሸንበቆው አንድ ነው” (ገጽ 78) በማለትም የቅማንትን አማራነት ታረጋግጣለች፡፡ ‹‹እንቧለሌ›› እንዲህ ያሉ ስስና ግዙፍ ፖለቲካዊ ጉዳዮችን በልቦለድ፣ ከልቦለድም በወግ መልኩ በማቅረቡ፣ ከማቅረቡም በላይ ርዕሰ-ነገሩን በሚገባ መንተንተንና በዝርዝር መዳሰስ ባለመቻሉ (ባለመፈለጉ) ክብደት ተሰጥቶት በምንጭነት ለመጥቀስ የማይመች መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ በጠቅላላ አነጋገር ብሄር “የዘር ቆጠራ አይደለም፤ በጊዜ እና በሁኔታዎች ሂደት ውስጥ የተፈጠረ የአንድ ህዝብ የጋራ ስነ-ልቦና ነው። ስለሆነም ቅማንት ዘሩን እንዴትም እና ወደየትም ቢቆጥር አማራ ነው” የሚል ጭብጥ ይዞ ይሟገታል። ለአቶ ነጋ ጌጤ በተለይ የተጻፈም ባይሆን የሁለቱ የብሄር ብያኔ የቀጥታ ተቃራኒ ነው። የአቶ ነጋን የብሄር ትርጓሜና አረዳድ ከተቀበልን፣ ቅማንትና
አማራ ሁለት የተለያዩ ብሄሮች ይሆናሉ። ‹‹እንቧለሌ›› ደግሞ ቅማንትም እንደ አገው አማራ ነው፤ በማለት ቅማንትን በአማራነት ውስጥ እንዳለ አንድ ንዑስ ማንነት አድርጎ ያቀርበዋል፡፡ ‹‹እንቧለሌ›› በአንድ በኩል ‹‹አማራነት ስነ-ልቦናዊ ስሜት›› ነው ቢልም፣ አጥንትና ደም ቆጠራ ጭምር መሆኑን እንደሚቀበል በተዘዋዋሪ “…የዘርና የቋንቋ ጉዳይ ብቻ እንዳልሆነ…” ›በማለት ይነግረናል፡፡ ጥቂት ዝቅ ብሎ ደግሞ “… ብሄር የሚባለውም የደም ጉዳይ ሳይሆን የጋራ ስነ-ልቦና የሚፈጥረው የህዝብ ጉባዔ ነው፡፡” በማለት ብሄርን በዘር ቆጠራ ለማቆም መሞከርን እንደማይስማማበት ይጠቁማል፡፡
ደራሲው ዘር እንደ ባህል፣እንደ ቋንቋ ወዘተ ሁሉ የብሄር ማንነት አንድ አምድ ሆኖ መቆሙን የሚቀበል ይሁን ወይም ዘር በብሄር ማንነት ውስጥ ድርሻ የለውም እንደሚል እርግጠኛ ሆኖ መናገር ያስቸግራል፡፡ ይህ ግራ መጋባትና ግራ አጋቢነት የደራሲው ብቻ ሳይሆን የአማራ ብሄርተኝነት አቀንቃኞች ሁሉ ይመስላል፡፡ ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ የኢትዮጵያ ፖለቲካ የስበት ማዕከል ሆኖ የቀጠለው አማራ ብሄርተኝነት፣ የብሄርተኝነቱን መጠነ-ስፋት መወሰንና ማሳወቅ አልቻለም፡፡ ይህ ክፍትነቱ አማራው ለኢትዮጵያዊነት ካለው ቀናኢነት ጋር ተደምሮ፣ የአማራ ብሄርተኝነት በአንድነት ኃይሉ የሚወሰድ ያደርገዋል፡፡ ይህ የደራሲው ከሁሉም ልሁን ማለት የብሄርተኝነቱን ዥዋዥዌ የሚጠቁም ነው ሊባል ይችላል፡፡ እነዚህን ሁለት የብሄር አረዳዶችና አፈታታቸውን ይዘን፣ የዚህ ጽሁፍ ዋና ጭብጥ የሚያርፍበትን ጨመቅ እንጠይቅ፡፡ ቅማንት አማራ ነው ወይ? የአማራ ብሄርተኝነት ከአጥንትና ደም ቆጠራ ያመለጠ የስነ-ልቦና አንድነት ነው፡፡ አለቃ ተክለየሱስ ዋቅጅራ “የጎጃም ዘር በሙሉ ከአባይ እስከ አባይ” በሚለው መጽሃፋቸው፤ የጎጃምን ዘር እገሌ እንቶኔን ወለደ በሚለው ተለምዷዊ የዘር ቆጠራ፣ የጎጃምን ማን መሆንና ኬት መጣነት አብራርተዋል፡፡ በእንዲህ ያለው የህዝቦች ድልድል በጎጃምና በቅማንት መካከል ያለው ልዩነት፣ በአገውና በወሎ መካከል እንዳለው ያለ ልዩነት ይሆናል፡፡ በዚህ የዘርን ቆጥሮ ማንነትን የመወሰን የብሄርነት አበያየን ወሎም፣ ሸዋም፣ ጎንደርም፣ ጎጃምም ራሳቸውን የቻሉ የተለዩ ህዝቦች ይሆናሉ፡፡ እንዲህ ከሆነ አማራ ማን ነው? ወይስ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ-ማርያም እንደሚሉት፤ አማራ የሚባል ብሄር የለም?
ድህረ-ነገር/ መደምደሚያ
በዚህ ጸሃፊ እምነት፣ ማንነት በይበልጥ ስነ-ልቦና ነው፡፡ ብሄርን ከሚያቋቁሙ መስፈርቶች ውስጥ የጋራ ስነ-ልቦና እጅግ ከፍተኛውን ድርሻ ይይዛል፡፡ በቁጥር ይሄን ያህል ብሎ በሂሳባዊ ስሌት ለመግለጽ ቢያስቸግርም የአንበሳውን ድርሻ ያህል ወይም ከዚያም የበለጠውን ያህል ወሳኝነት አለው፡፡ የኦሮሞም ሆነ የትግሬ ብሄርተኝነት የቆመው “እኔ ኦሮሞ ነኝ፣ እኔ ትግሬ ነኝ” በሚል ችካል ላይ እንጅ እገሌ እንቶኔን ወለደ በሚል ስሌት አይደለም፡፡ ማንነት ስሜት እንጅ ስሌት አይደለም። አማራነት ህዝቦች የሚጋሩት የጋራ ስነ-ልቦና እንጅ አጥንትና ደም ቆጠራ አይደለም፡፡ አማራነት በጊዜና በሁኔታዎች የረጅም ጊዜ ሂደት የተፈጠረ አንድ የጋራ ስነ-ልቦና ነው፡፡ ይህ ምን ማለት ነው?
ቅማንቱንም፣ አገውንም፣ ጎጃሜውንም፣ ጎንደሬውንም …ወዘተ እኩል አማራ የሚያደርግ፣ በመካከላቸው ያለውን ንዑስ ልዩነቶች የሚያስረሳ፣ የጋራ ስነ-ልቦና አላቸው ማለት ነው፡፡ ይህ የአማራ የጋራ ስነ-ልቦና ራሱ ምንድነው? የአንድ ህዝብ ስነ-ልቦና በተለያዩ መሰረቶች ላይ ሊቆም ይችላል። የሚያስተሳስራቸውን የጋራ ገመድ በጊዜ እና በሁኔታዎች ሂደት ይፈትላሉ፡፡ የእኛ ነው በሚሉት ወይም የእነሱ ነው በሚባል አንድ ወይም ብዙ መሆኖች ላይ ሊመሰረት ይችላል፡፡ የቅማንትም ሆነ የመንዝ፣ የብቸናም ሆነ የቋራ፣ የጋይንትም ሆነ የሳይንት፣ የአገውም ሆነ የወልቃይት አማራ እኩል የሚጋራው፣ የጋራ መገለጫው ትምክህተኝነትና ነፍጠኝነቱ ነው፡፡ የአማራ ሁሉ የጋራ ስነ-ልቦናው መሰረቱ ትምክህቱና ነፍጠኝነቱ ነው፡፡ የተቀሩት ሌሎች ሁሉ አማራውን ያለ ልዩነት፣ ትምክህተኛና ነፍጠኛ ነው ይሉታል፡፡ ይህ ማለት ግን አማራው ከትምክህተኝነቱና ነፍጠኝነቱ በቀር የሚጋራው የጋራ ታሪክ፣ ባህል፣ ቋንቋ …ወዘተ የለም ማለት አይደለም፡፡ የስነ- ልቦና አንድነቱ የተሸመኑበትን ዋና ድርና ማጎች ለመለየት ብቻ ነው፡፡ አማራው ራሱም በሴራ ፖለቲከኞች ፕሮፓጋንዳ ግራ ቢጋባም ትምክህተኛና ነፍጠኛ መሆኑን ያውቃል። አጤ ምኒልክን፣ አጤ ኃይለስላሴን፣ አጤ ቴዎድሮስን፣ በላይ ዘለቀን ….ወዘተ ሁሉ አማራ የሚያደርጋቸው እገሌ እንቶኔን ወለደ የሚል የዘር ቆጠራ አይደለም፡፡ ከፍ ያለ ትምክህተኝነታቸውና ይህን ትምክህተኝነታቸውን የሚያስጠብቁበት ነፍጠኝነታቸው ነው፡፡ በመሆኑም ቅማንትነት እንደ ጎጃሜነት፣ እንደ አገውነት ..ወዘተ ያለ ንዑስ ማንነት ነው፡፡ ቅማንት ወሎየው እንደሚሆነው ሁሉ አማራ ነው፡፡ አቶ ነጋ ጌጤ የተከተሉት የዘር ቆጠራ፣ የቅማንት ንዑስ ማንነት ስነ-ልቦና የሚቆምበት መሰረት ከሚሆን በቀር የቅማንትን አማራነት የሚያስቀር አይደለም፡፡ ቅማንት አማራ ነው፤ አርጎባው አማራ እንደሆነው ሁሉ፡፡
መውጫ
የአማራ ብሄርተኝነት የቆመባቸው ምሰሶዎች ናቸው የተባሉት ትምክህተኝነትና ነፍጠኝነት ምንድን ናቸው? በሚቀጥለው ሳምንት የምመለስበት ይሆናል፡፡

Read 3260 times