Print this page
Saturday, 09 December 2017 13:14

የሮማው ጳጳስ፤ አባታችን ሆይ ፀሎት ማሻሻያ ያስፈልገዋል አሉ

Written by 
Rate this item
(3 votes)

• “...lead us not into temptation” የሚለው አባባል ስህተት ነው ብለዋል።
      • በአማርኛ ሕትመቶች፣ “ወደ ፈተና አታግባን” ተብሎ እንደተተረጎመ ይታወቃል።

   አባታችን ሆይ ተብሎ የሚታወቀው ፀሎት እንዲሻሻል እንደሚፈልጉ የካቶሊክ ቤተክርስትያን ፓትርያርክ ፍራንሲስ፣ ለሮይተርስ ተናገሩ። “አባታችን ሆይ”፣ የዘወትር ፀሎት እንደሆነ በብዙዎች እንደሚታመንበት ሮይተርስ ጠቅሶ፣ በዚሁ ፀሎት ውስጥ፣ “...lead us not into temptation” የሚለው አባባል ስህተት እንደሆነ ፓትርያኩ አባ ፍራንሲስ እንደተናገሩ ትናንት ዘግቧል።
King James Version (KJV) ተብሎ በሚታወቀው ትርጉም ላይ “...lead us not into temptation” በሚል አገላለፅ ተተርጉሟል። ወደ ፈተና አትምራን እንደማለት ነው።
American Standard Version (ASV) ተብሎ በሚታወቀው ትርጉም ላይ ደግሞ “...bring us not into temptation” በሚል አገላለፅ ሰፍሯል። ወደ ፈተና አታድርሰን፣ ወደ ፈተና አታቅርበን፣ ወደ ፈተና አታስገባን... የሚል ተመሳሳይ ትርጉም የያዘ ነው።
ፓትርያርኩ አባ ፍራንሲስ፣ እነዚህ አባባሎች፣ በተሳሳተ አተረጓጎም ሳቢያ የተዛባ መልዕክት ያዘሉ ናቸው ብለዋል። ፈጣሪ ለፈተና ይዳርገናል የሚል የተዛባ መልዕክት የያዙ የተሳሳቱ አተረጓጎሞች እንዲስተካከሉ እፈልጋለሁ ሲሉም ተናግረዋል - ጳጳሱ። “...let us not into temptation” በሚል አባባል መስተካከል እንዳለባቸውም ጳጳሱ ገልፀዋል። ይህ አባባል፣ ከቀድሞዎቹ የእንግሊዝኛ ትርጉሞች የተለየ መልዕክት የያዘ እንደሆነ ተናግረዋል። ለፈተና አታጋልጠን፣ ከፈተና ጠብቀን፣ ከፈተና ከልለን አይነት መልእክት ይመስላል አተረጓጎሙ። እነዚህ አባባሎች፣ ከቀድሞው የአማርኛ ትርጉም፣ (ወደ ፈተና አታግባን ከሚለው አባባል) ጋር፣ የዚያን ያህል የተራራቀ መልዕክት ይዘዋል ለማለት ግን አስቸጋሪ ነው (... ወደ ፈተና አታስገባን... ከማለት ይልቅ... ወደ ፈተና አታግባን ተብሎ የተተረጎመ ከመሆኑ አንፃር)።
አባታችን ሆይ የሚለው ፀሎት በክርስትና መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ፣ በሁለት ቦታዎች የሰፈረ መሆኑን ዘገባዎቹ አያይዘው ገልፀዋል።
ማትዮስ 6፡9-13 የሰፈረው ፅሁፍ የመጀመሪያው ሲሆን፣ እንዲህ ይላል።
በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፣  ስምህ ይቀደስ፣ መንግስትህ ትምጣ፤
ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች፣ እንዲሁ በምድር ትሁን፤
የዕለት እንጀራችንን ዛሬ ስጠን፤
እኛም ደግሞ የበደሉንን ይቅር እንደምንል፣ በደላችንን ይቅር በለን፤
ከክፉም አድነን እንጂ፣ ወደ ፈተና አታግባን፤ መንግስት ያንተ ናትና ኃይልም ክብርም ለዘለዓለሙ፤ አሜን።
ሁለተኛውና አጠር ብሎ የቀረበው ደግሞ በሉቃስ ወንጌል የተፃፈው ነው።
ሉቃስ 11፡2-4
በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፣  ስምህ ይቀደስ፣ መንግስትህ ትምጣ፤ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች፣ እንዲሁ በምድር ትሁን፤
የዕለት እንጀራችንን ዕለት በዕለት ስጠን፤
ኃጢአታችንንም ይቅር በለን፣ እኛ ደግሞ የበደሉንን ሁሉ ይቅር ብለናልና፤ ከክፉም አድነን እንጂ፣ ወደ ፈተና አታግባን።

Read 8528 times
Administrator

Latest from Administrator