Saturday, 13 January 2018 15:06

የመኢአድን ልሣን ጋዜጣ “አንብበዋል፤ አስነብበዋል” የተባሉ ታሠሩ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(4 votes)

 በደቡብ ክልል ደራሼ ወረዳ፣ የመኢአድን ልሣን ጋዜጣ አንብበዋል፤ አስነብበዋል የተባሉ የአመራር አባላት መታሰራቸውን ፓርቲው አስታወቀ፡፡
መኢአድ ሰሞኑን በሰጠው መግለጫ፤ ከተቋረጠ ከረጅም ዓመታት በኋላ ወደ ህትመት የተመለሰው “አንድነት” የተሰኘውን የድርጅቱን ልሣን ጋዜጣ “አንብባችኋል፤ አስነብባችኋል” በሚል የፓርቲው የማዕከላዊ ም/ቤት ሃላፊና የወጣቶች ጉዳይ ሃላፊ በወረዳው አስተዳደር መታሰራቸውን ጠቁሟል፡፡
የአመራር አባላቱ “ጋዜጣውን ለምን አከፋፈላችሁ” ተብለው ለእስር መዳረጋቸውን የገለፀው መኢአድ፤ የድርጅቱ ልሣን የሆነው “አንድነት” ጋዜጣን ማሠራጨት እንደማይቻል ከወረዳው እንደተገለፀለት አስታውቋል፡፡
በደራሼ ወረዳው በሚገኝ አንድ ጠጅ ቤት ውስጥ ጋዜጣውን ሲያነቡ የተገኙ ግለሰቦችም ጋዜጣው ከእጃቸው እየተነጠቀ መቀደዱን የተናገሩት የመኢአድ ም/ፕሬዚዳንት አቶ ሙሉጌታ አበበ፤ ጋዜጣውን ሸጠዋል የተባሉት የፓርቲው አመራሮች ደግሞ መታሠራቸውን አመልክተዋል፡፡
በደቡብ ክልል የፓርቲ አመራሮቻችንና አባሎቻችንና ወከባ እየተፈፀመባቸው ነው ያሉት አቶ ሙሉጌታ፤ በተለይ ጋዜጣቸውን ወደ ክልሉ ለማሰራጨት መቸገራቸውን ገልፀዋል፡፡

Read 5123 times