ዩኒቨርሲቲ በገቡ በወራት ጊዜ ውስጥ ዶክትሬቱ እንደተሰጣቸው ተነግሯል
የዚምባቡዌ የጸረ-ሙስና ኮሚሽን፣የቀድሞው የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሮበት ሙጋቤ ባለቤት የሆኑት ግሬስ ሙጋቤ፣ ከዩኒቨርሲቲ ኦፍ ዚምባቡዌ ተቀብዬዋለሁ የሚሉት የዶክትሬት ዲግሪ ህገ-ወጥ ነው በሚል ጥርጣሬ ጉዳዩን መመርመር መጀመሩን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ ጸረ-ሙስና ኮሚሽን፣ የቀድሞዋ ቀዳማዊት እመቤት ግሬስ ሙጋቤ፣ የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ያገኙት በአግባቡ መሆንና አለመሆኑን ለማጣራት ምርመራ የጀመረው፣ የዩኒቨርሲቲ ኦፍ ዚምባቡዌ መምህራን፣ ጉዳዩን እንዲያጣራላቸው ፊርማ በማሰባሰብ ባለፈው ሳምንት ያቀረቡለትን ጥያቄ መሰረት አድርጎ ነው ተብሏል፡፡
ግሬስ ሙጋቤ ምንም እንኳን በ2014 ወደ ዩኒቨርሲቲው ገብተው እንደነበር ቢነገርም፣ የዶክትሬት ዲግሪያቸው የተሰጣቸው ግን እንደ ሌሎች ተማሪዎች አመታትን የፈጀ ምርምር ካደረጉና ብቃታቸውን ካረጋገጡ በኋላ ሳይሆን ወደ ዩኒቨርሲቲው በገቡ በወራት ጊዜ ውስጥ ነው መባሉን ዘገባው አመልክቷል፡፡
የዩኒቨርሲቲው መምህራን ግሬስ ሙጋቤ፣ ምርምር ሳያደርጉና በመዛኞች ብቃታቸው ሳይረጋገጥላቸው ዶክትሬታቸውን ማግኘታቸውን ለኮሚሽኑ ባቀረቡት ማመልከቻ ጠቁመዋል ያለው ዘገባው፤ ግሬስ ከዚህ ቀደም የትምህርት ማስረጃቸውን ትክክለኛነት በተመለከተ ለሚቀርቡባቸው ጥርጣሬዎች መሰረተ ቢስ ናቸው የሚል ምላሽ ይሰጡ እንደነበርም አስታውሷል፡፡