Saturday, 27 January 2018 12:06

የውጭ ጉዳይ ሚ/ር፤ 21 ኢትዮጵያውያንን ከሊቢያ አስመለሰ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(1 Vote)


    የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከዓለማቀፉ የስደተኞች ድርጅት (IOM) ጋር በመተባበር፣ 21 ኢትዮጵያውያንን ከሊቢያ ወደ ሃገር ቤት ማስመለሱን ያስታወቀ ሲሆን 45 ኢትዮጵያውያንም ወደ አገራቸው ለመመለስ ተዘጋጅተዋል ብሏል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጽ/ቤት ለአዲስ አድማስ ባደረሰው መግለጫው፤ከተመለሱት 21 ኢትዮጵያውያን መካከል 16ቱ ሴቶች መሆናቸውንና ጥቂቶቹም በእስር ላይ እንደነበሩ ጠቁሟል፡፡ ተመላሽ ኢትዮጵያውያኑ በትሪፖሊና በቤንጋዚ የነበሩ መሆናቸውን የጠቆመው የቃል አቀባዩ ጽ/ቤት፤ ኢትዮጵያውያኑ በስቃይ ውስጥ የቆዩ እንደመሆናቸው የህክምና አገልግሎት ተደርጎላቸዋል ብሏል፡፡
መንግስት በሊቢያ የሚገኙና ወደ ሀገር ቤት ለመመለስ ፍቃደኛ የሆኑ ኢትዮጵያውያንን ለመመለስ የተቻለውን ሁሉ ጥረት ያደርጋል ያሉት የውጭ ጉዳይ ቃል አቀባይ አቶ መለስ አለም፤ በዋናነት የማስመለሱን ተግባርም ካይሮ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ እያከናወነ ነው ብለዋል፡፡
በሊቢያ አፍሪካውያን በባርነት እየተሸጡ መሆኑ በአለማቀፍ መገናኛ ብዙኃን መገለፁን ተከትሎ በርካቶችን አስደንግጦ እንደነበር የሚታወስ  ሲሆን ኢትዮጵያውያንም የዚህ የባሪያ ንግድ ሰለባ መሆናቸው ታውቋል፡፡
በሌላ በኩል በሳኡዲ አረቢያና በሱዳን እስር ቤቶች ውስጥ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን መንግስት እንዲታደጋቸው ተደጋጋሚ ጥሪ እያቀረቡ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡   

Read 2145 times