Saturday, 03 February 2018 13:18

ካናዳ ከብሄራዊ መዝሙሯ 2 ቃላት ትቀይራለች

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

   (ጾታዊ እኩልነት ለመፍጠር)

    የካናዳ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ ከ37 አመታት በላይ በድምቀት ሲዘመር በዘለቀውና “ኦ… ካናዳ” የሚል ርዕስ ባለው የአገሪቱ ብሄራዊ መዝሙር ውስጥ የሚገኙትን ጾታዊ እኩልነትን ያላማከሉ ቃላት ለመቀየር የቀረበለትን ረቂቅ የውሳኔ ሃሳብ ከሰሞኑ አጽድቆታል፡፡
በካናዳውያን መካከል ጾታን መሰረት ያደረገ ልዩነት የሚፈጥርና ሁሉንም ዜጎች ያማከለ መሆን ሲገባው ለወንዶች ያደላ ነው በሚል ከ8 አመት በፊት ጀምሮ ቅሬታ ሲቀርብበትና ሲያነጋግር ቆይቷል ይላል ቢቢሲ - በእንግሊዝኛ ቋንቋ በተዘጋጀው የአገሪቱ ብሄራዊ መዝሙር ግጥም ውስጥ የሚገኘውን አንድ ነጠላ ሃረግ፡፡
“በሁሉም ወንድ ልጆችሽ ፈቃድ…” የሚለው ይህ የብሄራዊ መዝሙሩ ግጥም አካል የሆነ ሃረግ፣ “በእናት ካናዳ ጉዳይ የሚያገባቸው ወንድ ልጆቿ ብቻ ናቸው” የሚል የተዛባና ጾታዊ እኩልነትን ያላማከለ መልዕክት ያዘለ በመሆኑ፣ ቃላቱ ተቀይረው ከጾታ ክፍፍል በጸዳ ሌላ ስንኝ ይተካ በሚል የቀረበውን ቅሬታ መሰረት በማድረግ፣ በጉዳዩ ላይ ድምጽ የሰጠው ምክር ቤቱ፣ የስንኙ ሁለት ቃላት እንዲቀየሩና “በሁላችንም ፈቃድ” የሚል ትርጉም እንዲሰጥ ወስኗል፡፡
“ኦ ካናዳ” የሚለው የአገሪቱ ብሄራዊ መዝሙር በይፋ ስራ ላይ የዋለው እ.ኤ.አ በ1980 እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ ከዚያ ጊዜ አንስቶ በነበሩት ዓመታትም፣ “ወንድ ልጆችሽ” የሚለውን አገላለጽ የያዘው ይሄው አነጋጋሪ ሃረግ እንዲቀየር የሚጠይቁ የውሳኔ ሃሳቦች ለ12 ጊዜያት ያህል ለምክር ቤቱ ቀርበው እንደነበርና ሁሉም ሳይጸድቁ መቅረታቸውን አስታውሷል፡፡

Read 1847 times