Monday, 05 February 2018 00:00

የኬንያ ነገር - ሁለት መሪ፣ አንድ አገር!

Written by 
Rate this item
(0 votes)

  “አንቺም አባዎራ እኔም አባዎራ
                   ግራ ገባው ቤቱ በማ እንደሚመራ…”

   በኬንያ ከወራት በፊት በተካሄደው የድጋሚ ምርጫ ያሸነፉት ኡሁሩ ኬንያታ፤ በይፋ ቃለ መሃላ ፈጽመው አገሪቱን በፕሬዚዳንትነት መምራት ከጀመሩ ከወራት በኋላ፣ እነሆ ያልተጠበቀ ነገር ባለፈው ማክሰኞ በመዲናዋ ናይሮቢ ተከናወነ፡፡
ምርጫው ተጭበርብሯል ብለው ካስደገሙ በኋላ፣ ራሳቸውን ከውድድሩ ያገለሉት የተቃዋሚው ፓርቲ መሪ ራይላ ኦዲንጋ፤ ባለፈው ማክሰኞ ናይሮቢ በሚገኝ ፓርክ ውስጥ በሺህዎች የሚቆጠሩ ደጋፊዎቻቸውን ሰብስበው፣ “የታላቋ ኬንያ ሪፐብሊክ  ፕሬዚዳንት ነኝ” ሲሉ በማወጅ ቃለ መሃላ ፈጸሙ፡፡
የያዘውን ስልጣን በድንገት መነጠቁ ያስደነገጠውና ጉዳዩ ወደ ከፋ ግጭት እንዳያመራ ያሰጋው የኡሁሩ ኬንያታ መንግስት፤ የጎንዮሹ ቃለ መሃላ አገርን የሚያፈርስ፣ክፉ ድርጊት በመሆኑ እንዳይካሄድ ብሎ ቢያስጠነቅቅም፣ ራይላ ኦዲንጋ ግን ጆሮ ዳባ ልበስ ብለው፣ መጽሃፍ ቅዱሳቸውን ከፍ አድርገው ይዘው፣ መሪነታቸውን አወጁ። ሁለተኛ ፓርላማ ማቋቋማቸውንም በድፍረት ተናገሩ፡፡
ህጋዊው የኡሁሩ መንግስት. የኦዲንጋን የጎንዮሽ በዓለ ሲመት በቀጥታ ስርጭት ለህዝቡ ለማድረስ እየተዘጋጁ የነበሩትን ኬቲኤን፣ ኤንቲቪ እና ሲቲዝን ቲቪ የተባሉ ሶስት ታላላቅ የአገሪቱ የቴሌቪዥን ጣቢያዎችን ስርጭት አቋርጧል፡፡
የኡሁሩ መንግስት የቴሌቪዥን ጣቢያዎቹን መዝጋቱን ተከትሎ፣ ባለፈው ሃሙስ የአገሪቱ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ችሎት ላይ ተሰይሞ ጉዳዩን ካጤነው በኋላ፣ ለ14 ቀናት ያህል በጉዳዩ ዙሪያ ቀጣይ ምርምራ አድርጎ እስከሚጨርስና የመጨረሻ ብይን እስኪሰጥ ድረስ፣ የመንግስት ውሳኔ ተሽሮ፣ የቴሌቪዥን ጣቢያዎቹ ስርጭታቸውን እንዲቀጥሉ ወስኗል፡፡
የኡሁሩ መንግስት ግን የፍርድ ቤቱን ውሳኔ አክብሮ፣ ጣቢያዎቹን ለመክፈት ፍላጎት አለማሳየቱን የዘገበው ቢቢሲ፤ የአዲሱ ፕሬዚዳንት ራይላ ኦዲንጋ ደጋፊዎችና ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዲሁም የአገሪቱ በርካታ ጋዜጠኞች፣ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ ህገ መንግስታዊ መብትን የሚጥስ ነው፣ በማለት የመንግስትን እርምጃ ማውገዛቸውን አመልክቷል፡፡
የኡሁሩ ኬንያታ መንግስት ለጉዳዩ ተገቢውን ትኩረት ሰጥቶ ሁነኛ ምላሽ እስካልሰጠ ድረስ፣ ኬንያ በቀጣዮቹ ቀናት ወደ ከፋ ብጥብጥና ቀውስ ልታመራ እንደምትችል የሚናገሩት የመብት ተሟጋቾች፤ ሁለቱም ሃይሎች አገሪቱን ወደ ጥፋት ከማምራት እንዲቆጠቡ ጥሪ ማቅረባቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

Read 2846 times