Sunday, 11 February 2018 00:00

29 ስደተኛ ኢትዮጵያውያን በኬንያ ፖሊስ ታሰሩ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

  53 ኢትዮጵያውያን ከሞዛምቢክ እስር ቤት ወጥተዋል

    የኬንያ መንግስት በህገ ወጥ መንገድ ወደ ግዛቴ ገብተዋል ያላቸውን 29 ኢትዮጵያውያን፣ ከትናንት በስቲያ ሐሙስ ጠዋት ያሰረ ሲሆን በሌላ በኩል፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ በሞዛምቢክ በህገ ወጥ መንገድ ድንበር አቋርጠዋል ተብለው የታሰሩ 53 ኢትዮጵያውያንን ማስፈታቱን  አስታውቋል፡፡
ፓስፖርትና አስፈላጊ የጉዞ ሰነዶች ሳይኖራቸው፣ ከሞያሌ በጭነት መኪና በመጓጓዝ ላይ ሳሉ ሩዋራካ በተሰኘች የኬንያ ግዛት ውስጥ በቁጥጥር ስር የዋሉት 29 ኢትዮጵያውያን፣ አላማቸው ወደ ደቡብ አፍሪካ መሻገር እንደነበር  የኬንያው ዘ ስታንዳርድ ጋዜጣ  ዘግቧል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ በፖሊስ ቁጥጥር ስር በዋሉበት ወቅት የተሻለ ስራ ፍለጋ ከሀገራቸው መሰደዳቸውን መናገራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ በእስረኞች ማቆያ እንዲገቡ ተደርጎም፣ ተጨማሪ ምርመራ እየተደረገባቸው መሆኑን አመልክቷል፡፡
ከኢትዮጵያውያኑ በተጨማሪ የመኪናው አሽከርካሪ በቁጥጥር ስር ዋለ ሲሆን የኬላ ጠባቂ ፖሊስ ላይም ምርመራ እየተካሄደ ነው ተብሏል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ፍ/ቤት ከቀረቡ፣ በህገ ወጥ መንገድ የሀገሪቱን ግዛት በማቋረጥ ወንጀል ተከሰው፣ እስከ 1 ዓመት የሚደርስ እስራት ሊፈረድባቸው እንደሚችል ታውቋል፡፡  
በሌላ በኩል፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ በተመሳሳይ የሞዛምቢክን ድንበር በህገ ወጥ መንገድ አቋርጠው ደቡብ አፍሪካ ሊገቡ ሲሉ በሞዛምቢክ ፖሊስ ተይዘው ታስረው የነበሩ 53 ኢትዮጵያውያንን፣ ከፍተኛ ድርድር በማድረግ ማስመለሱን አስታውቋል፡፡ ከወራት በፊትም በተመሳሳይ፣ በዛምቢያ እስር ቤት የነበሩ 150 ኢትዮጵያውያንን በማስፈታት፣ ወደ ሀገር ቤት እንዲመለሱ ማድረጉን ሚኒስቴሩ መግለፁ ይታወሳል፡፡    

Read 3295 times