Sunday, 18 February 2018 00:00

የአውስትራሊያ ምክትል ጠ/ሚ፣ በወሲብ ቅሌት ሳቢያ ስልጣን ሊለቁ ነው

Written by 
Rate this item
(2 votes)

   የአገሪቱ መሪ፤ ሚኒስትሮች ከባልደረቦቻቸው ጋር ፍቅር እንዳይጀምሩ አስጠንቅቀዋል

   ከሰሞኑ ይፋ ከተደረገባቸው የወሲብ ቅሌት መረጃ ጋር በተያያዘ፣ አገራዊ የመነጋገሪያ አጀንዳ የሆኑት የአውስትራሊያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ባርናቢ ጆይስ፤ የፓርቲ መሪነትና የሚኒስትርነት ስልጣናቸውን ይለቃሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የተዘገበ ሲሆን የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ማልኮም ተርንቡልም፤ ሚኒስትሮች ተመሳሳይ ድርጊት ፈጽመው ከተገኙ ከፍተኛ ቅጣት እንደሚጠብቃቸው ማስጠንቀቃቸው ተዘግቧል፡፡
የአገሪቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ባርናቢ ጆይስ፣ በቅርቡ የ24 አመት ትዳራቸውን በማፍረስ፣ የስራ ባልደረባቸው ከሆነች አንዲት ሴት ጋር በፈጠሩት የድብቅ የፍቅር ግንኙነት፣ ሴትየዋን ማስረገዛቸውን የሚያጋልጥ የወሲብ ቅሌት መረጃ ከሰሞኑ ይፋ መደረጉንና ጉዳዩ ትልቅ አገራዊ አጀንዳ መሆኑን የዘገበው ዘ ቴሌግራፍ፤ ይህን ተከትሎም የአገሪቱ ፓርላማ ከትናንት በስቲያ ባደረገው ስብሰባ፣ ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ ተከስተዋል ያላቸውን ሌሎች ተጨማሪ የሙስና ድርጊቶችን በመመርመር፣ ሚኒስትሩ ከስነምግባር ውጭ የሆነና ክብርን የሚያጎድፍ ጸያፍ ተግባር በመፈጸማቸው፣ በፈቃዳቸው ስራቸውን እንዲለቅቁ ወይም እንዲባረሩ የሚጠይቀውን የውሳኔ ሃሳብ በአብላጫ ድምጽ ማጽደቁን አመልክቷል፡፡
“በምክትል ሚኒስትሩ ድርጊት እጅግ አዝኛለሁ፤ ይሄም ሆኖ ግን ከአሁን በኋላ ባለትዳርም ሆነ ወንደላጤ ማንኛውም ሚኒስትር፣ የስራ ባልደረባው ከሆነች ሴት ጋር በፍጹም የፍቅር ግንኙነት መመስረትም ሆነ አንሶላ መጋፈፍ አይችልም” ሲሉ በይፋ ያስጠነቀቁት የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ማልኮም ተርንቡል፤ ድርጊቱ በቀጣይም እንደ አንድ ከባድ የስልጣን ብልግና ወይም የሙስና ወንጀል ተወስዶ እንደሚያስቀጣም አስታውቀዋል፡፡
ምንም እንኳን በአገሪቱ የሚኒስትሮች ስነምግባር ደንብ ውስጥ ከስራ ባልደረባቸው ጋር የፍቅር ግንኙነት በሚጀምሩም ሆነ በሚያማግጡ ሚኒስትሮች ዙሪያ የሚያትት ምንም አይነት አንቀጽ ባይኖርም፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግን ከአሁን በኋላ መሰል ድርጊት የፈጸመ ሚኒስትር፤ ከፍተኛ ቅጣት እንደሚጠብቀው በማስጠንቀቅ፣ ድርጊቱን በግልጽ የሚያወግዙና ተገቢ ቅጣት የሚጥሉ ህጎችና መመሪያዎች በቀጣይ ወጥተው፣ ተግባራዊ እንደሚደረጉም ተናግረዋል፡፡
24 አመታትን በትዳር አብረዋት ከዘለቋት ባለቤታቸው፣ አራት ሴት ልጆችን ያፈሩት የ50 አመቱ የአገሪቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር፤ የስራ ባልደረባቸው ከሆነች ሌላ ሴት ጋር በድብቅ እፍ ክንፍ ማለታቸውና ማስረገዛቸው ባለፈው ሳምንት ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ ጉዳዩ የአገሪቱን ፖለቲካ ፓርቲዎችም ጨምሮ በርካታ ዜጎችን እያነጋገረ እንደሚገኝም ዘገባው አስታውሷል፡፡  

Read 1780 times