Sunday, 25 February 2018 00:00

ዓለማቀፉ ማህበረሰብ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን እንዴት ተቀበለው?

Written by 
Rate this item
(0 votes)

    ከየካቲት 9 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ ለሚቀጥሉት 6 ወራት በአገሪቱ ላይ የተጣለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብና የምዕራብ መንግስታት፣በጥርጣሬና በስጋት ነው የተቀበሉት፡፡ የአሜሪካ መንግስትና የአውሮፓ ህብረትም፤አስቸኳይ ጊዜ አዋጁን አስመልክቶ ያወጡት መግለጫ ከወትሮው የተለየ ነው፡፡  
አዋጁን በፅኑ የተቃወመው የአሜሪካ መንግስት በኤምባሲው በኩል ባወጣው መግለጫ፤ “የኢትዮጵያ መንግስት በተለይ በመሰብሰብና ሀሳብን በነፃነት በመግለጽ መብት ላይ ገደብ የሚጥለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጁ፣ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተፈጠረውን ሁሉን አሳታፊ የሆነ የለውጥ መነሳሳት የሚያቀጭጭ፣ ይሰፋል ተብሎ በተስፋ የሚጠበቀውን የፖለቲካ ምህዳርም የበለጠ የሚያጠብ ነው” ብሏል፡፡   
 “የተፈጠሩት ሁከቶችና ብጥብጦች የሰው ህይወትን እየቀጠፉ እንደሆኑና በዚህም መንግስት ጭንቀት ውስጥ መግባቱን እንገነዘባለን” ያለው ኤምባሲው፤“ሆኖም ለዚህ አይነቱ ችግር መፍትሄው  መብትን መገደብ ሳይሆን የበለጠ ነፃነትን መፍቀድ ነው” ብሏል -የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን መውጣት አጥብቆ እንደሚቃወመው በመግለጽ፡፡
የአውሮፓ ህብረት በበኩሉ፤መንግስት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጁ እየተካሄደ ያለውን የፖለቲካ ማሻሻያ በእጅጉ የሚጎዳ ነው ብሏል - በመግለጫው፡፡  
“አዋጁ መልካሙን ጅምር ሊያጠፋው ይችላል፤ከተቻለ የአጭር ጊዜያት ቆይታ ይኑረው” ሲልም ለመንግስት ምክር ለግሷል - ህብረቱ፡፡  
አዋጁ በሚተገበርባቸው ጊዜያት መሰረታዊ የሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩና መሰረታዊ መብቶች እንዲረጋገጡ የአውሮፓ ህብረት የጠየቀ ሲሆን ለሀገሪቱ ሁነኛ የፖለቲካ መፍትሄ ሊሆን የሚችለው ከተቃዋሚዎችና ከሀገሪቱ የፖለቲካ ተዋናዮች ጋር የሚደረግ  ውይይት ነው ተብሏል፡፡
በኢትዮጵያ የኔዘርላንድ አምባሳደር ቤንት ቫን በሰጡት አስተያየት፤አዋጁ የሰብአዊ መብቶችን እንዳይገድብ ስጋት አለን ብለዋል፡፡ የአዋጁ የቆይታ ጊዜ ማጠር የሚችልበት ሁኔታም መመቻቸት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡
“ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስልጣን ለመልቀቅ መወሰናቸው በበጎ የሚታይ ቢሆንም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የዜጎችን የመናገር፣ የመሰብሰብና ሃሳብን የመግለፅ መብቶች የሚገድብ በመሆኑ ያሳስበኛል” ያለው ደግሞ የእንግሊዝ መንግስት ነው፡፡  
አዋጁ ለአጭር ጊዜ ብቻ ይተገበራል የሚል ተስፋ አለኝ ያለው የእንግሊዝ መንግስት፤ “በዚህ ጊዜ ውስጥም ቢሆን መንግስት መሰረታዊ የዜጎችን ሰብአዊ መብቶች ያከብራል የሚል እምነት አለን” ብሏል፡፡ “በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወቅትም ሰዎችን በጅምላ ማሰርና ኢንተርኔትን ማቋረጥ ሊተገበር አይገባም” ሲል አሳስቧል - የእንግሊዝ መንግስት የአፍሪካ ጉዳዮች ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ፡፡
“የኢትዮጵያ መንግስት ሰላማዊ፣ ፈጣንና ግልፅነት በተሞላው መንገድ የለውጥ ሂደቱን ለማስቀጠል አዲሱን ጠቅላይ ሚኒስትር ይመርጣል ብለን ተስፋ እናደርጋለን” ያለው መግለጫው፤ “ስለ ወዳጅነታችንም ለኢትዮጵያውያን እርዳታችን አይለይም” ብሏል፡፡
በሌላ በኩል ከተለያዩ የዓለም ሀገራት አምባሳደሮች ጋር በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ላይ ሰሞኑን ውይይት ያደረጉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ፤”አዋጁ ሀገሪቱ የገጠማትን የሰላምና መረጋጋት ችግር ለመፍታት የተዘጋጀ ነው፣ ተግባራዊ ከተደረገ ወዲህም የሀገሪቱ ሁኔታ መሻሻል አሳይቷል” በማለት የአዋጁን ጠቀሜታ ለዲፕሎማቶቹ አስረድተዋል፡፡   

Read 3175 times