Saturday, 03 March 2018 11:53

የአድዋው ድል - አባት

Written by  ደረጀ በላይነህ
Rate this item
(2 votes)

ይወሳ ጀግናው ምኒልክ፣ መከታሽ የቁርጥ ቀኑ
የአንድነት ዋልታ ማገሩ፣ አስተዋይ ሀቅ ሚዛኑ፡፡
ትዘከር ቆራጥዋ ንግሥት፣ ጣይቱ የብልሃት መልህቅ
በፍልሚያ የተሰለፈች፣ ነፃነት ክብርሽ እንዲልቅ።
በዜጎች አጥንትና ደም፣ ታሪክሽ ተቀሰተ
ጦቢያ ሆይ ኩሪ ክበሪ፣ ድመቂ ዘመን በባተ፡፡
ከደራሲ፣ ገጣሚ ፀሐይ መላኩ “አድዋና ምንይልክ” ግጥም ላይ የተቀነጨበ ነው። ገጣሚዋ እንደ ማናችንም የአድዋ ድል ታሪክ አካላትና የትሩፋቱ ተካፋዮች የድል ምሰሶ አፄ ምኒልክ መሆናቸውን፣ በስንኞችዋ መስክራለች። ሌላው ደግሞ የስነ ጋብቻና የሥነ ልቡና ምሁራን እንደሚስማሙበት፤ ብልህዋና ጀግናዋ ባለቤታቸው እቴጌ ጣይቱም ለንጉሠ ነገሥቱ ጥንካሬና ድል፣ ትልቅ ሚና መጫወትዋን ገጣሚዋ መስክራለች። እኔም ትልቁ አሜሪካዊ ገጣሚ ዋልት ዊትማን እንደሚለው፤ “ሴት ልጅ የወንድን ልጅ ሰብዕና ትቀርፃለች” በሚለው እስማማለሁ፡፡ እቴጌ ጣይቱ ለአድዋው ድል በግንባር ቆማ ካደረገችው የጀግንነት ተጋድሎ ባሻገር፣ ምኒልክን በማማከር ሃሳብ በማዋጣት፣ ለዘመናይቱ ኢትዮጵያ ደማቅ አሻራ አስቀምጠዋል ብዬ አምናለሁ፡፡
በጠላቶቻቸው ሳይቀር የተመሰከረላቸው ብልሁና አስተዋዩ መሪ ንጉሠ ነገሥት ምኒልክ፤ ለዚህ ዓለም አቀፋዊ የታሪክ መዘክርነታቸው፣ አስተዋፅኦ አደርገዋል ብዬ የማስበውና የማምነው ሌላም ታላቅ ንጉሠ ነገሥት አሉ፡፡ እኒህም በመቅደላ ላይ ለሀገራቸው ክብርና ልዕልና ከእነህልማቸው በክብር ያለፉት አፄ ቴዎድሮስ ናቸው፡፡
ንጉሥ ምኒልክ ከ11 እና 12 ዓመት ዕድሜ እስከ ሃያ ያለውን ያሳለፉት በአፄ ቴዎድሮስ ቤተ መንግስት ነው፡፡ የስነ ልቡና ምሁራን እንደሚሉት፤ እኔም ኤልሳቤጥ ቢ ሀርሎክ ከፃፉት መጽሐፍ እንደተጋራሁት፤ ስለ ህይወት፣ ስለ እምነት፣ በአጠቃላይ ስለ ቀጣዩ ዘመን ህይወት አቅጣጫቸው ነገሮችን የሚፈትሹበትና የሚጨብጡበት ጊዜ ነው። ስለዚህም አጠገባቸው፣ አካባቢያቸው ካሉት ነገሮች ለህይወት ዘመናቸው መልክና ማንነትና ቅርፅ የሚያወጡት ይሄ ነው፡፡
“Adolosence depend upon their sex, their intellegence, the environment in which they live, the opportunities they have had for developing interests.
ንጉሠ ነገሥት ምኒልክ ካደጉበት አካባቢና ቤተ መንግሥት፣ በዚህ ዕድሜያቸው ያገኙትና የቀሰሙት ነገር አለ ብዬ የማምነውም በዚህ የተነሳ ነው፡፡ በታሪክ እንደምናውቀው አፄ ቴዎድሮስ ህልማቸው አንድነትና ሥልጣኔ ነበር፡፡ የመጨረሻ ህልፈተ ህይወታቸውም ለቴክኖሎጂና ሥልጣኔ ካላቸው ናፍቆት ጋር ተያይዞ፣ ከእንግሊዛውያኑ የጠበቁትን ነገር በማጣታቸው በተፈጠረ ግጭት ነው፡፡ ታዲያ በምኒልክ ልብ ከዚህ ይበልጥ ሊቀረፅ የሚችል ናፍቆት አልነበረም፡፡ እናም ይህንን በጥሩ ያስቀመጡትን ህልም ዙፋን ላይ ሲቀመጡ በተግባር አውለውታል፡፡ ምናልባት ጀግንነቱ በአፄ ምኒልክ ልብ ይበልጥ ደምቆ የተሳለባቸው ይሄኔ ነው - የሚል ግምት አለኝ፡፡
የአፄ ምኒልክ ትዕግስት ግን ከአፄ ቴዎድሮስ ፈጣን ቁጣ ጋር በእጅጉ ይራራቃል፡፡ ይህንንም በሌላ መንገድ ለይተን ብንጠረጥር የሚል ሀሳብ አለኝ፡፡
አፄ ቴዎድሮስ ውስጥ የነበረ ያ ግዙፍ ህልም፣ ዘመኑና ማህበረሰቡ፣ እምነቱን ፍልስፍናው የፈጠረው፣ ያ ታላቅ ራዕይ፣ በምን እንደከሰመ ያዩት ምኒልክ፣ ከአፄ ቴዎድሮስ ይልቅ ታጋሽነት ያዋጣኛል! ብለው አምነው፣ ያደረጉት ነገር ቢሆንስ የሚል ግምት አለኝ፡፡ ብቻ በዚያም አለ በዚህ በአፄ ምኒልክ ልብ ውስጥ የቴዎድሮስ ህልም ተፀንሶ አድጓል፡፡ ከዚያም በኋላ ሀገርንና አህጉርን የሚያኮሩ ታላላቅ ስራዎች ወደ መሬት ወርደዋል፡፡ ሀገራቸው፣ ለዚህ ወሮታም በየጊዜው እልል እያለች ታደንቃቸዋለች፡፡
በተለይ ከአድዋው ጦርነትና ድል ጋር ምኒልክን ስናስባቸው ታላቅ አስተዋይና መልካም መሪም እንደሆኑ እናያለን፡፡ የጦር ባለሟሎቻቸውና ራሶቻቸው ሳይቀር፤ “ከእርስዎ በፊት እኔን ያስቀድመኝ! የሚል ልብ እንደነበራቸው፣ የሀገራችንና የውጭ ሀገር ፀሐፍት መስክረዋል። ለዚህ ዋቢ የምናደርገው ታላቁን የጦር መሪ አሉላ አባነጋን ነው፡፡ አሉላ፤ “ፍላጎቴ ለአፄ ምኒልክ የጦርነት ድግሥ ሳይሆን የሰላም ድግስ እንዲጠብቃቸው ነው” ብለዋል፡፡ ግድ ካልሆነ ምኒልክ ጦርነት ውስጥ እንዳይገቡ ይፈልጋሉ፡፡ ይህ የሚያሳየው መሪው በተከታዮቻቸው ውስጥ ያኖሩትን ታማኝነትና ፍቅር ነው፡፡ ይህ ደግሞ በአመራር ሳይንስ ውስጥ ትልቁ ሥራ ነው፡፡ የስነ - አመራር ሳይንስ ምሁር፣ የበርካታ መጽሐፍት ደራሲ የሆኑት ጆን ሲ ማክስዌል፤ “የአንድ መሪ ታላቅነት የሚለካው፣ በሚያፈራቸው መሪዎች ልክ እንደሆነ አፅንኦት ይሰጣሉ፡፡
በስነ - አመራር ሳይንስ ውስጥ አዕማድ የሆኑት የአመራር ሞዴል፣ ፍልስፍናና ዘይቤ፣ አንዱ ውስጥ ያለው በሌላኛው ላይ ሊደረብ ይችላል፤ ብለው ያምናሉ፡፡ ለምሳሌ ሞዴሎቹ ውስጥ ምኒልክ Trait based በሚለው መታገጊያ ውስጥ ልንመድባቸው እንችላለን፡፡ ከላይ የጠቀስነው አስተዳደግና ክህሎት እያለም፤ ንጉሱ የተወደዱ መሪ ናቸው፡፡ ምክንያቱም ይህ የአመራር ዘይቤ፤ አንድ መሪ ለመሪነት ይወለዳል፣ በሚለው ያምናል፡፡ የሰውየውን፣ ወይም የመሪውን ሰብዕና መሰረት ያደርጋል፡፡ ስለዚህም ይህ ሞዴል “Personality profile of an effective leader” ይባላል፡፡
የዘመናችን የዘርፉ ምሁራን፤ መሪ በመወለድ ሊገኝ የሚችልበትንና አጋጣሚ ወደ አሥራ አምስት ፐርሰንት ዝቅ ቢያደርጉት እንኳ መሪ የሚኮነው፣ በመሪዎች በጎ ተፅዕኖ ነው የሚለውን ብቻ መውሰድ በእጅጉ ይከብዳል፡፡ ለምሳሌ ታላቁ አሜሪካዊ ፖለቲከኛና ዲፕሎማት ቤንጃሚን ፍራንክሊን፤ ከልጅነቱ ዕድሜ ጀምሮ በየትኛውም ቦታ መሪ እንደነበር ግለታሪኩን ሲፅፍ በጉልህ አስፍሮታል። በተጨማሪ ታላቁ ጦረኛ ጄኔራል ናፖሊዮን ቦናፖርትም፤ ገና በእንጭጭ ዕድሜ በነበረውና በሚያሳየው ጠባይ፤ ቤተሰቦች የጦር ሰውና መሪ ሊሆን እንደሚችል በመገመት፣ ወደ ጦር አካዳሚ አስገብተውታል፡፡ ውጤቱንም ታሪክና የዓለም ህዝብ ሁሉ ያውቀዋል፡፡
ለኔ ዳግማዊ አፄ ምኒልክ Trait base leader ናቸው - ለመሪነት የተወለዱ፡፡
ለጊዜው ከላይ ካየነውና ከአመራር ሞዴል ከወሰድነው አንድ ነጠላ ዘርፍ አለፍ ስንል፤ የአመራር ዘይቤን በሚመለከት ደግሞ ከሶስቱ ሞዴሎች ማለትም ካሪዝማቲክ፣ ትራንስፎርሜሽናል ናርሲስቲክ ውስጥት በካሪዝማቲክ ሊደር (ተቀባይነትና ሞገሥ ያላቸው) መሪ ብለን ልንፈርጃቸውና ምናልባትም ባንዳንድ የአመራር ሁኔታቸው፣ አንዳንዴ የትራንስፎርሜሽናል መሪን አካሄድ ይቀይጣሉ ማለት እንችላለን፡፡
ካሪዝማቲክ መሪ ለሚለው መነሻው ዘመነ አርስቶልና ግሪክን ማሰብ ግድ ይላል፡፡ የቃሉም መነሻ  በግሪክ “Kharis” ሲሆን ፀጋ፣ ሞገስ፣ ከፈጣሪ የተሰጠ ወደ ሚለው ይወስደናል፡፡ በዘመናዊው አስተሳሰብ ደግሞ ታላቅ ጥበብ፣ ውስጣዊ ብርሃን፣ አርአያነት፣ በቀጣዩ ዘመን ስላለው ህልምና፣ ግብ በእጅጉ ጠንካራ አቋም ያለው እንደማለት ነው፡፡
ምኒልክ በእጅጉ ብልህ፤ አስተዋይ፤ ይቅር ባይና አትንኩን ባይ ነበሩ፡፡ ይህ ሁሉ በዚህች ሀገር አደባባዮች ተፈትኗል፡፡ እነ ኦሬስቲ ባራቲዮሬ (ኤርትራ ውስጥ የነበረው የጣሊያን ጦር አዛፕላሰ-ፔዮትሮ ቶዜሊ፣ ኢትዮጵያን ቅኝ በመግዛት ምኞት ሰክረው፤ ከሀገራቸው መሪዎች በተቀበሉት ምክርና ህልም የሁለቱን ሀገራት ግንኙነት ሲንጡ፣ ምኒልክ በፍፁም ትዕግስትና ሠላማዊ አካሄድ የሁለት ሀገራት መንገድ እየጠበቁ፣ በሌላ በኩል ግን ጦራቸውን ያደራጁ ነበር፡፡ ከዚያም ሌላ የንጉሠ ነገሥቱ አፄ ዮሐንስ ልጅ ራስ መንገሻ በሸፈቱባቸውም ጊዜ ያሣዩት መለሳለሥና በኋላም ከጣሊያን ጋር አብረው፣ ጣሊያን የከዳቸው ራስ መንገሻ በምህረት ሲመለሱ ያደረጉላቸው አቀባበል፤ የምኒልክን ብልህነትም መልካምነት የሚያሣይ ነው። በአጠቃላይም ሲታይ፣ የአድዋው ጦርነት በድል መጠናቀቁና ከ100 ሺህ በላይ ሠራዊት በፈቃደኝነት ማሰለፍ መቻላቸው፡፡ የዚህ በሣል አመራር ውጤት ነው፡፡
ምኒልክን ከትራንስፎርሜሽናል መሪ ጋር የሚያጎዳኛቸው፣ የሚመሯቸውን ሰዎች ማሣተፋቸውና ብልሃት ፈጣሪ መሆናቸው ነው። በተለይ ትልልቅ ውሣኔዎችን ለመወሰን፤ የራሶቻቸውንና ፊታውራሪዎቻቸውን ድምፅ ይሰማሉ፡፡ በመጨረሻው ጊዜም ከጦርነቱ ማግስት፣ በከሀዲዎችና በጣሊያን ምርከኞች ላይ ሊወሠድ ስለሚገባው እርምጃ እነ ራስ አሉላ አባ ነጋን ሰብስበው የመከሩት የዚህ ዐይነቱ የተሻለና ዘመናዊ መሪ ስለነበሩ ነው፡፡ ምኒልክ ዕድሜያቸው አርባ ዘጠኝ ዓመት ስለነበር፣ ብስለታቸው የብዙ ነገሮች ውጤት ነው፡፡
እንደ ማሳረጊያ ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን “ምኒልክ” ከሚለው ተውኔቱ ጥቂት ስንኞች እዋሳለሁ፡-
“እምቢ አለ ምኒልክ እምቢ አለ?”
“አንቀፅ አሥራ ሰባት
በቃል ትርጉም ክፋት
ባሥለኮሰው እሳት
የአባ ዳኜን ብልሀት
ከቶም ለማሳሳት
አልቻለም ፈፅም!..
አንቶኒሊ አጣም
ቢሸርብ አዳክሞ
አልቻለም ፈፅሞ…!”

Read 3462 times