Print this page
Saturday, 03 March 2018 16:00

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፓርላማ ፀድቋል

Written by 
Rate this item
(16 votes)

 • “ኮማንድ ፖስቱ የተለጠጠ ሥልጣን ተሰጥቶታል”
    
   ለ6 ወር የሚተገበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት በ2/3ኛ ድምፅ የፀደቀ ሲሆን የአዋጁን ድንጋጌዎች ተላልፎ የተገኘ እስከ 5 ዓመት በሚደርስ እስራት ይቀጣል ተብሏል፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በ346 ድጋፍ፣በ88 ተቃውሞና በ7 ድምጸ ተአቅቦ ጸድቋል ተብሎ ነበር፡፡ ሆኖም በኋላ ላይ በተሰጠው መግለጫ፤አዋጁ በ395 የድጋፍ ድምጽ ጸድቋል በሚል ተስተካክሏል፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን የተቃወሙት በአብዛኛው የኦሮሚያ ክልል ተመራጭ የፓርላማ አባላት መሆናቸውም ታውቋል፡፡
ጠቅላይ አቃቤ ህግ አቶ ጌታቸው አምባዬ፤ የአዋጁን አስፈላጊነት ባብራሩበት ንግግራቸው፤ በዋናነት አዋጁ ትኩረት ያደረገው የፀጥታ ችግሮችን ከመሰረቱ ማድረቅ ላይ ነው ብለዋል፡፡ ግጭቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሱ አድማሳቸው እየሰፋ መጥቷል ያሉት አቶ ጌታቸው፤ የዜጎች የመንቀሳቀስ መብት፣ በፈለጉበት ቦታ ተዘዋውሮ የመኖርና ሃብት አፍርቶ የመጠቀም መብትን የሚገድቡ እንቅስቃሴዎች ተበራክተዋል፣ አሳሳቢ ደረጃም ደርሰዋል ብለዋል፡፡
አሁን እየተከሰቱ ያሉ ሁከቶች ኃይል የተቀላቀለበት የሰው ህይወት የሚቀጠፍበት፤ ብሄርን መነሻ በማድረግ ዜጎችንም የሚያፈናቅል ሆኗል ተብሏል። በሌላ በኩል በከተሞች ህገ ወጥ የመሬት ወረራዎች መበራከታቸውንም አቶ ጌታቸው ጠቁመዋል፡፡
አዋጁም እነዚህን ችግሮች ከምንጩ ለማድረቅ ታቅዶ የተዘጋጀ ነው ብለዋል፡፡ ለዚህም ሲባል ከዚህ ቀደም ከነበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በተለየ ሁኔታ በዋናነት የሚተኮረው የሁከት ጠንሳሾችና አቃጆች ላይ ይሆናል ተብሏል፡፡
ሌላው አዋጁ በዋናነት ትኩረት የሚያደርገው የተፈናቀሉ ወገኖችን ወደ ነበሩበት ለመመለስ የሚደረግን ጥረት ማገዝ ላይ ይሆናል ያሉት አቶ ጌታቸው፤ ህዝባዊ አገልግሎት በሚሰጥባቸው የስፖርት ማዘውተሪያ ስታዲየሞችና የሃይማኖት ተቋማት የመሳሰሉት አካባቢ የሚፈጠሩ ሁከቶችን መቆጣጠር ላይ ትኩረት ይደረጋል ብለዋል፡፡
ህገ ወጥ የመሬት ወረራንና ግንባታን እንዲሁም የኢንቨስተሮችን መሬት በህገ ወጥ መንገድ መውሰድን መከላከል ላይ አዋጁ ያተኩራል ተብሏል፡፡
በአዋጁ ማብራሪያ ላይ አስተያየትና ጥያቄ ያቀረቡ በርካታ የምክር ቤት አባላት፤ በተለይ በአዋጁ አፈፃፀም ላይ በየደረጃው ያሉ የክልል የአስተዳደር አካላት ድርሻ ሊኖራቸው ይገባል ያሉ ሲሆን በተለያዩ አንቀፆች ላይም ማሻሻያዎችን ጠይቀዋል፡፡
የምስራቅ ወለጋ ዞን የፓርላማ ተመራጭ ባቀረቡት አስተያየት፤ በነቀምት ከተማ ተከስቶ ከነበረው ግጭትና ተቃውሞ ጋር ተያይዞ የዞኑ ም/አስተዳዳሪና የነቀምት ከተማ ከንቲባ መታሰራቸውን በመጥቀስ፤ በዚህ አዋጅ አስተዳደሮች ሰለባ ከመሆን ይልቅ አብረው መስራት ቢችሉ የተሻለ ነው ብለዋል፡፡
አንድ አባልም አዋጁ ለ6 ወር ከሚፀና ወደ 3 እና 4 ወር ዝቅ ቢል የሚል አስተያየት ሰንዝረዋል፡፡
የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ከመስጋት አንፃር አዋጁ በህዝቡ ተቀባይነት ላያገኝ ይችላል የሚል ስጋት እንዳላቸው የገለፁ አንድ የምክር ቤት አባል “ማንኛውም የመገናኛ ዘዴ ሊቋረጥ ይችላል” የሚለው ድንጋጌም በመገናኛ ብዙኃን ህልውና ላይ ችግር ሊፈጥር ይችላል የሚል ስጋት ተፈጥሯል” ብለዋል፡፡
እኚሁ የምክር ቤቱ አባል፤ ህገ ወጥ የመሬት ወረራ የተመለከቱ ጉዳዮች በመደበኛ ህግ ሊታዩ ይችላል የሚል ሃሳብ አቅርበዋል፡፡
“ኮማንድ ፖስቱ የተለጠጠ ሥልጣን ነው የተሰጠው” ያሉ ሌላው የምክር ቤት አባል በበኩላቸው፤ “ኮማንድ ፖስት ከመሬት ጋር ምን አገናኘው?” ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ በህዝባችን ላይ ስጋት የፈጠረው የተለጠጡ መብቶች ለኮማንድ ፖስቱ መሰጠቱ ነው ሲሉ አክለዋል፡፡
ከምክር ቤቱ አባላት ለተነሱት ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ የሰጡት ጠቅላይ አቃቤ ህጉ፤ በአሁኑ ወቅት ሁከትና ብጥብጥ እየተጠራ ያለው በማህበራዊ ሚዲያ መሆኑን በመጥቀስ፤ መገናኛ ዘዴዎችን መቆጣጠር የሚያስችል ሁኔታ ለኮማንድ ፖስቱ ካልተፈቀደ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ትርጉም አይኖረውም ብለዋል፡፡
ከመሬት ጋር በተያያዘ በመደበኛ ህግ፣ ህገ ወጥ የመሬት ወረራን የክልልና የፌደራል አስተዳደሮች ማስቆም ባለመቻላቸው በአዋጁ መካተቱን የጠቀሱት አቶ ጌታቸው፣ “ህግና ስርዓት የለም በሚል መሬት የሚወረርበትና ህገ ወጥ ግንባታ የሚከናወንበት ሁኔታ ተፈጥሯል” ብለዋል፡፡
“የኢንቨስተሮች መሬትን መቀማትም በህግና በስርአት መሆን አለበት ከዚህ ውጪ ያለ እርምጃ በቸልታ አይታለፍም” ብለዋል - ጠቅላይ አቃቤ ህጉ፡፡
አዋጁ፤ “የወንጀል ተጠያቂነትን” ባስቀመጠበት አንቀፁ፤ “መደበኛ ህግ የተመለከተው እንደተጠበቀ ሆኖ በዚህ አዋጅ የተመለከቱ ከአስቸኳይ ጊዜ እርምጃዎችና መተባበር ጋር የተያያዙ ግዴታዎችን ተላልፎ የተገኘ ማንኛውም ሰው እስከ አምስት ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት ይቀጣል” ይላል፡፡   


=========

ከጋዜጣው አዘጋጅ፡-  በፓርላማ የተገኘው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ፤አዋጁ በ346 የድጋፍ ድምጽ መጽደቁን የዘገበ ሲሆን በኋላ ላይ የፓርላማው ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር የድጋፍ ድምጹ 395 ነው በሚል ማስተካከያ መስጠታቸው ይታወቃል፡፡ ሆኖም በጋዜጣው ላይ 390 የድጋፍ ድምጽ የሚል የቁጥር ስህተት ተፈጥሯል፡፡ ለዚህም ውድ አንባቢያንን ይቅርታ ልንጠይቅ እንወዳለን፡፡
 



  

Read 8010 times Last modified on Saturday, 03 March 2018 17:41
Administrator

Latest from Administrator