Sunday, 18 March 2018 00:00

የፍ/ቤት ውሳኔ ተፈፃሚ አልሆነም ሲሉ ካህናቱ ምሬታቸውን ገለጹ

Written by 
Rate this item
(5 votes)

  “በመልካም አስተዳደርና በፍትህ እጦት እየተንገላታን ነው”

     ያለ አግባብ ከቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪነታችን ተባረናል፣ ደሞዝም ተቋርጦብናል ያሉ ካህናት፤ በፍ/ቤት ተከራክረን ብንረታም ፍርዱ ሳይፈፀምልን እየተጉላላን ነው ሲሉ ምሬታቸውን ገልጸዋል፡፡
መልአከ ገነት ኃ/ማሪያም ቦጋለ እና መጋቢ ሃይማኖት መንግስቱ ድረስ፣ በ2009 ዓ.ም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ የአዲስ አበባ ሃገረ ስብከት መንፈሳዊ ፍ/ቤት ባቀረቡት አቤቱታ፤ከህግ አግባብ ውጪ ከስራቸው መባረራቸውንና ደሞዛቸውን ተከልክለው ለችግር መዳረጋቸውን የገለጹ ሲሆን ፍ/ቤቱም አቤቱታቸው ተገቢነት ያለው ነው ብሎ ወደ ስራ መደባቸው እንዲመለሱ፣ደሞዝም እንዲቆረጥላቸው ውሳኔ ማሳለፉን ይናገራሉ፡፡  
የፍ/ቤቱ ውሳኔ በሚያዚያ 2009 ዓ.ም የተሰጠ ቢሆንም እስከ ዛሬ ድረስ ለዓመት ገደማ ተፈጻሚ እንዳልሆነ ለአዲስ አድማስ የጠቆሙት ካህናቱ፤በአዲስ አበባ ሃገረ ስብከት ከፍተኛ በደል እየተፈፀመብን ነው ብለዋል፡፡ ጉዳያቸው ፈጣን እልባት እንዲያገኝ ለፓትርያርክ ፅ/ቤት አመልክተው የፍ/ቤቱ ውሳኔ በአስቸኳይ እንዲፈፀምላቸው ትዕዛዝ ቢሰጥም እስካሁን በትዕዛዙ መሰረት ወደ ሥራቸው አለመመለሳቸውን ተናግረዋል - ካህናቱ፡፡   
 የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን በጉዳዩ ጣልቃ እንዲገባ አቤቱታ ማቅረባቸውንም የጠቆሙት ካህናቱ፤ኮሚሽኑ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ነሐሴ 1 ቀን 2009 ዓ.ም በፃፈው ደብዳቤ፤ የፍርድ ቤቱ ውሳኔ እንዲከበርና ካህናቱ ወደ ስራ መደባቸው እንዲመለሱ በማሳሰብ፣ይህ ሳይሆን ከቀረ ትዕዛዙን ባልፈፀሙት ወገኖች ላይ የህግ እርምጃ እንደሚወሰድ ቢገለፅም ይህም ተቀባይነት አላገኘም ብለዋል፡፡
ከዚህ በኋላ ጉዳያችንን ወዴት አቤት እንደምንል አናውቅም የሚሉት ካህናቱ፤በመልካም አስተዳደርና በፍትህ እጦት እየተንገላቱ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡  

Read 2248 times