Sunday, 18 March 2018 00:00

ሊቢያ 205 ህገወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች እንዲታሰሩ አዘዘች

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

 የተለያዩ የአፍሪካ አገራት አምባሳደሮች በወንጀሉ ተሳትፈዋል ተብሏል

    የሊቢያ መንግስት አፍሪካውያንን በአስቸጋሪውና ሞት በበዛበት የሜዲትራኒያን ባህር በኩል ወደ አውሮፓ አገራት ለአመታት በማጋዝ ከፍተኛ ሃብት ሲያካብቱ ነበር ባላቸው 205 ህገወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች ላይ የእስር ትዕዛዝ በማውጣት በቁጥጥር ስር ለማዋል ዘመቻ መጀመሩን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የእስር ትዕዛዝ የወጣባቸው እነዚሁ ህገወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች የሊቢያና የሌሎች አገራት ዜጎች መሆናቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ተፈላጊዎቹ ከህገወጥ የሰዎች ዝውውር በተጨማሪ በስደተኞች ላይ ግድያ፣ ግርፋትና የአስገድዶ መድፈር ወንጀሎችን በመፈጸም ክስ እንደሚመሰረትባቸውም አመልክቷል፡፡ የሊቢያ መንግስት ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ እንዳለው፤ የእስር ትዕዛዝ ከተላለፈባቸው ተጠርጣሪዎች መካከል የሊቢያ የደህንነት ቢሮ አባላት፣ የስደተኞች ወህኒ ቤቶች ሃላፊዎችና በሊቢያ የሚገኙ የተለያዩ የአፍሪካ አገራት ኤምባሲዎች አምባሳደሮች እንደሚገኙበትም ዘገባው አስረድቷል፡፡ ስውር የህገወጥ የሰዎች ዝውውር ሰንሰለት በመዘርጋት፣ ለአመታት በተደራጀ ሁኔታ በርካታ አፍሪካውያን ስደተኞችን ከፍተኛ ገንዘብ በማስከፈል በአስቸጋሪ የባህር ጉዞ ለሞትና ለስቃይ ሲዳርጉና አሰቃቂ ጥቃቶችን ሲፈጽሙ ነበር የተባሉት እነዚሁ ተጠርጣሪዎች፤ ከአሸባሪው ቡድን አይሲስ ጋር ግንኙነት አላቸው መባሉንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

Read 1744 times