Tuesday, 20 March 2018 11:24

የአዳም ረታ አዲስ መፅሐፍ ማክሰኞ ይመረቃል

Written by 
Rate this item
(3 votes)

  “…እንደጥንት ዘመዶቼ ወይ እንደዛሬዋ እማማ በየደጀሰላሙ አልጎዘጎዝም፡፡ በቅዱስ መጽሐፍት ቸርቻሪዎች አልጠፈርም፡፡ እዛ ፔርሙዝ ውስጥ ያለው ሻይ ሳይሆን ደም ነው ብልህ አንተ ምን አገባህ? አንቺስ? አሥራት ሁሉን ዝቅና ከፍ ለእኔ ትታ ተኝታለች፡፡ ከንፈሮቿ ስስ ቅጠል ይመስላሉ። የታችኛው ለአመል አበጥ ይላል፡፡ በእኔ በኩል ያለው ቀለሙ ሙሉ በሙሉ አለቀቀም፡፡ በቀስታ እጄን ሰድጄ በአመልካች ጣቴ ያን ለአመል ያበጠ ቦታ ነካሁት፡፡ ዐይኖቿን በትንሹ ገልጣ ፈርጠም አለች። ቀኝ እጇን አንስታ በዳበሳ ፊቴን ነካችኝ፡፡ ጣቴ ከንፈሯ ላይ መሆኑን ረሳሁ፡፡ ዐይኖቿን ስትገልጥ አቡሽ እወድሃለሁ እኮ … መቼ ይገባሃል? አለችና ወደ በለጠ ጥልቅ እንቅልፍ ለመግባት አይነት ተመቻቸች፡፡…” (አዳም ረታ አፍ፤ 205)
በተለየ የአፃፃፍ ብቃትና ዘይቤው የሚታወቀው አንጋፋው ደራሲ አዳም ረታ “አፍ” የተሰኘ አዲስ ረዥም ልብ ወለድ መፅሐፍ ለአንባቢያን የበቃ ሲሆን የፊታችን ማክሰኞ ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በብሔራዊ ቴአትር እንደሚመረቅ የምርቃቱ አዘጋጅ ኢጋ ሚዲያና ኮሙኒኬሽን ገለፀ፡፡
በምርቃት ስነ-ስርዓቱ ላይ ደራሲውን ጨምሮ በርካታ አድናቂዎቹ፣ ደራሲያንና ገጣሚያን የሚታደሙ ሲሆን በመፅሐፉ ላይ ዳሰሳ ይቀርባል። ከዚህም በተጨማሪ ግጥምና ወግ እንዲሁም ከመፅሐፉ የቀነጨቡ ታሪኮች ይነበባሉ፡፡ ደራሲው አዳም ረታም በመፅሐፉ ዙሪያ ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጥ ይጠበቃል፡፡ በ254 ገፆች የተቀነበበው መፅሃፉ፤ በ80 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም “ማህሌት”፣ “ግራጫ ቃጭሎች”፣ “አለንጋና ምስር”፣ “እቴሜቴ የሎሚ ሽታ”፣ “ከሰማይ የወረደ ፍርፍር”፣ “ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ”፣ “ህማማትና በገና”፣ “መረቅ” እና “የስንብት ቀለማት” የተሰኙ መፅሐፍቶችን ለንባብ አብቅቷል፡፡

Read 8689 times