Print this page
Sunday, 13 May 2018 00:00

ፎርብስ የአመቱን የዓለማችን ሃያላን ይፋ አደረገ

Written by 
Rate this item
(3 votes)

ዢ ጂፒንግ በወንዶች፣ አንጌላ መርኬል በሴቶች ቀዳሚነቱን ይዘዋል

    ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፤በ2018 የፈረንጆች አመት በተለያዩ መስኮች ተጠቃሽ አለማቀፍ ተጽዕኖ ፈጥረዋል ያላቸውን 75 የዓለማችን ሃያላን ዝርዝር ይፋ ያደረገ ሲሆን በወንዶች የቻይናው ፕሬዚዳንትና የኮሙኒስት ፓርቲ ዋና ጸሃፊ ዢ ጂፒንግ፣ በሴቶች የጀርመኗ መራሂተ መንግስት አንጌላ መርኬል ቀዳሚነቱን ይዘዋል፡፡
ላለፉት አራት ተከታታይ አመታት፣ የፎርብስ የአለማችን ቁጥር አንድ ሃያል ሆነው የዘለቁት የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ዘንድሮ ቦታቸውን ለዢ ጂፒንግ አስረክበው፣ ወደ ሁለተኛ ደረጃ ዝቅ ያሉ ሲሆን የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሶስተኛነት ይከተላሉ፡፡
የአመቱ የአለማችን ቁጥር አንድ ሃያል ሴት የተባሉት የጀርመኗ መራሂተ መንግስት አንጌላ መርኬል፣ ከአለማችን ሃያላን የአራተኝነት ደረጃን መያዛቸውን የጠቆመው የፎርብስ መግለጫ፤ የአለማችን ቁጥር አንድ ባለጸጋ ጄፍ ቤዞስ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል፡፡
የሮማው ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ፣ የማይክሮሶፍቱ መስራች ቢል ጌትስ፣ የሳዑዲው ልዑል ሞሃመድ ቢን ሳልማን አል ሳኡድ፣ የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲና የጎግል ኩባንያ መስራች ላሪ ፔጅ እንደ ቅደም ተከተላቸው፣ ከስድስተኛ እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡
በዘንድሮው የፎርብስ የአለማችን ሃያላን ዝርዝር ውስጥ 17 ሰዎች ለመጀመሪያ ጊዜ የተካተቱ ሲሆን፣ ተራማጅ እንደሆኑ የሚነገርላቸው የሳዑዲ አረቢያው ልዑል ሞሃመድ ቢን ሳልማን አል ሳኡድ፣ ከእነዚህ አዲስ ገቢዎች አንዱ ናቸው፡፡
በአመቱ የአለማችን ሃያላን ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱ ታዋቂ ግለሰቦች መካከል 13ኛ ደረጃን የያዘው የፌስቡኩ መስራች ማርክ ዛከርበርግ፣ 36ኛ ደረጃን የያዙት የሰሜን ኮርያው መሪ ኪም ጁንግ ኡን፣ 66ኛ ደረጃን የያዙት የአፍሪካ ቁጥር አንድ ቢሊየነር ናይጀሪያዊው አሊኮ ዳንጎቴ እና 73ኛ ደረጃን የያዙት የአሸባሪው ቡድን አይሲስ መሪ አቡበከር አል ባግዳዲ ይገኙበታል፡፡
ፎርብስ የፖለቲካ ተጽዕኖ ፈጣሪነት፣ ተሰሚነት፣ የሃብት መጠን፣ የስኬት ደረጃና የመሳሰሉትን መስፈርቶች በመጠቀም ከገመገማቸውና በዝርዝሩ ውስጥ ካካተታቸው የአመቱ ሃያላን መካከል የአገራት መሪዎች፣ የኩባንያ ባለቤቶችና የስራ ሃላፊዎች፣ የተቋማትና ቡድኖች መሪዎች ወዘተ ይገኙበታል፡፡

Read 3149 times
Administrator

Latest from Administrator