Saturday, 04 August 2018 10:27

“ዕድሜ ለእኔ በል! እሥር ቤት ውስጥ እኔ ስገርፍ እያየህ፤ ከአንድ እስከ ዐርባ ቁጥር ተማርክ”

Written by 
Rate this item
(13 votes)

 ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አዳኝ ሰው ወፎች እያጠመደ ይኖር ነበር፡፡ አንድ ቀን አንዲት የወርቅ ቀለም ያለው ላባ ያላት ወፍ አጠመደ፡፡ ለብዙ ቀናት የወፍ መኖሪያ መረብ ሰርቶ ምግብ እያከማቸና እየቀለበ ካስቀመጣት በኋላ አንድ ቀን፤
“ወፌ ሆይ! እስከዛሬ ስቀልብሽ እንደነበርኩ ታስታውሻለሽ፣ አይደል?” አለና ጠየቃት፡፡
ወፊቱም፤
“አዎን ጌታዬ! ተንከባክበህ፣ አሳምረህ አኑረኸኛል፡፡ ወደፊትም ታኖረኛለህ የሚል ሙሉ ዕምነት አለኝ!” ስትል መለሰች፡፡
“ግን ወፌ!” አለና ጀመረ አዳኙ ጌታዋ፤ “አሁን ሁለት ነገር ለማድረግ እፈልጋለሁ፡፡ ሁለተኛው የወርቅ ላባሽን መሸጥና መጠቀም ነው፡፡ የመጀመሪያው ደግሞ ላባሽን በቁምሽ መንጨትና መሸጥ ስለማልፈልግ፤ አርጄ እበላሻለሁ፡፡ ከዚያ ላባሽን እሸጠዋለሁ! ሌላ ምንም ለማድረግ አልችልም!” አላት፡፡
ወፊቱ ጥቂት ካሰበች በኋላ፤
“ጌታዬ ሆይ! ያልከው ዕውነት ነው፡፡ ሆኖም አንተ ካሰብከው በላይ ጠቃሚ የሆነ ነገር እሰጥሃለሁ”
“ምን?” አለ ጌትየው፡፡
“አየህ፤ የእኔን ሥጋ መብላትም ሆነ የወርቅ ላባዬን መሸጥ ያለው ጥቅም የአንድ ጊዜ ብቻ ነው፡፡ እኔ የምሰጥህ ነገር ግን ዘለዓለም የምትጠቀምበት ነው፡፡”
“ምንድን ነው የምትሰጪኝ?”
“ምክር”
“ምን ምክር?” አለ በጉጉት፡፡
“ሦስት ምክሮችን ነው የምለግስህ፡፡ አንደኛውን እዚሁ እጅህ ላይ ሳለሁ እነግርሃለሁ፡፡
ሁለተኛውን አቅራቢያችን ካለው ዛፍ ላይ ሆኜ እነግርሃለሁ፡፡ ሦስተኛውን አየር ላይ ሆኜ አበስርሃለሁ።”
አዳኙ በሀሳቧ ተስማማና፤
“እሺ፤ የመጀመሪያውን ንገሪኝ” አላት፡፡
ወፊቱም፤ “የመጀመሪያው ምክሬ፤ የማታገኘውን ነገር አትመኝ! የሚል ነው”
አዳኙም፤ “ጥሩ፤ ሁለተኛውን ንገሪኝ” አለና ወደ ዛፉ እንድትሄድ ለቀቃት፡፡
ወፊቱም እየበረረች ዛፉ ላይ አረፈች፡፡ ከዚያም፤ “በእጅህ የገባውን ነገር በጥንቃቄ ያዝ፤ አትልቀቅ” ብላው ወደ አየር ከነፈች፡፡
ይሄኔ አዳኙ በጣም ተናዶ፤
“ወይኔ! ወይኔ! አንቺን መልቀቅ አልነበረብኝም፡፡” እያለ ፀጉሩን ሲነጭ፤
“አሁን ሶስተኛውን ምክሬን ልንገርህ” አለችና ከንዴት አስቆመችው፡፡
“ሦስተኛውን ምክርሽን ልስማ እሺ?” አለ፡፡
ወፊቱም፤
“ባለፈ ነገር አትፀፀት” ብላ ወደ ህዋ አንደኛዋን መጠቀች፡፡
***
የወፊቱ ምክሮች በአሁኑ ወቅት ለእኛ የሚሆኑ ናቸው፡፡ የማናገኛቸውን ነገሮች መመኘት አይኖርብንም። የምንመኘውን ነገር ለማግኘት አቅማችንን፣ ጊዜውንና አካሄዳችንን ከምር ማስላትና ማውጠንጠን አለብን። አለበለዚያ፤
“ምኞቴ እንደጉም መንጥቃ
ተስፋዬ እንደጉድፍ ወድቃ
የወንድሜን ልጆች እንኳ፣ ላባት ርስት ሳላበቃ
የእኔ ነገር በቃ በቃ …” ብለን እንቀራለን (ፀጋዬ ገ/መድህን፣ የከርሞ ሰው፤ አብዬ ዘርፉ)
ቀጥሎ በልቦናችን ሊመዘገብ የሚገባው፣ በእጃችን ያለውን አጥብቀን መያዝን ነው፡፡ ኢትዮጵያ በጀመረችው የለውጥ ጉዞ እያገኘችና እያስመዘገበች ያለው ድል የእስካሁን ዕድሜው አጭር ከመሆኑ በስተቀር አመርቂና ዘላቂ እንደሚሆን፣ ተስፋው እጅግ ያማረ ነው! ይህንን ድል መጠበቅና ተጠንቅቆ መያዝ ተገቢ ነው!! ምነው ቢሉ፤ አንሸራታች ደለልና “ያፋፍ ላይ ድጥ” መቼም ቢሆን ሊያጋጥም ይችላልና! በመሰረቱ፤ ማናቸውም ወደፊት የሚጓዝ ክስተት ከአሮጌ ሥርዓት ጋር መጋጨቱም ሆነ፤ ግራ የተጋባው የህብረተሰብ ክፍል መንገዱና መንፈሱ ሲያቀዣብረው፤ እንደ ተራ ምቀኝነትም ራሱ የሌለበት ነገርና ያልቃኘው ክራር የማይጥመው ወገን መኖሩ፤ ከቶም አስገራሚ አይደለም! እኒህን “የአውቆ አበድም ሆነ የአብዶ - አወቅ” ክፍሎች ወይም ወቅትን በወግ በወጉ አድርገው ለመጠቀም ያልቻሉ ወገኖችን፤ አግባብና ጥንቃቄ ባለው አያያዝ ማቀፍ ብልህነት ነው!
ማንም ጅል የማይስተው ጉዳይ ግን፣ አመራር የሆነ አካል ከጥበብና ከብልሃት ውጪ በሌላ ጎርበጥባጣ ፖለቲካዊ መንገድ እፈታዋለሁ ማለት ዘበት እንደሆነ ነው! ቀሳውስቱን፣ ምሁር ዳያስፖራውን፣ ተቃዋሚውንና በምንም ሰበብ ከሀገር የወጣውን ዜጋ ወደ ቤቱ፣ ወደ ቀዬው፣ ወዳገሩ ሊመልስ የሚችል ዕውቀት፣ ጥበብና ፍቅር ካለን፤ የውስጥ ቅራኔን ለመፍታት እንዴት መላ እናጣለን?! በእጃችን የያዝነውን እናጥብቅ!!
ሶስተኛው ወፋዊ ምክር፡- ባለፈ ነገር አለመፀፀት ነው፡፡ ከትላንትና መላቀቅ! በዕውቀት ያለፈውን መፍታት!!፡፡ ሀገራዊ ዕርቅን በጥንቃቄ ማስፋፋት!! ነገን መሻማት፡፡ ቢቻል ከነገ መስረቅ! (Plagarizing the future)
ዛሬ የኢትዮጵያን ለውጥ ለማምጣት በሚደረገው ሙከራ ውስጥ አንዱ ዓይነተኛ ተግባር ከአናት የተቃኘ ዲሞክራሲን ማስወገድ ነው (Guided democracy እንዲሉ)፡፡ እስካሁንም ዲሞክራሲያዊ አካሄድ እንዲሽመደመድ ያደረገው፤ “ይሄው በልካችሁ የተሰፋ ዲሞክራሲ እኔ ልስጣችሁ” የሚል አባዜ ነው፡፡ ከወዲሁ የከረረውን የማላላት፣ ፅንፍ ይዞ የሚጓዘውን ሃይ የማለት፣ ተቋሚነትን በህብረተሰብ ተሳትፎ የመገንባት ጠንካራ ስራ ይጠብቃል፡፡ ህዝብ “ጉዳዩ የእኔ ነው” እንዲል፣ ውሎ አድሮም የፈረሱን ልጓም እንዲጨብጥ ማድረግ ቀዳሚ እሳቤ መሆን ይኖርበታል፡፡ “እኔ ነኝ ያደረኩለት ዓይነት” አመለካከት፣ ህዝብ አያውቅም ወደሚል ክፉ ግምት ስለሚጥል አደገኛ ነው፡፡ አለበለዚያ፤ በ“እናት ዓለም ጠኑ” የፀጋዬ ገ/መድህን ቴያትር ውስጥ ተውኔታዊ ግነት ባለው መልኩ እንደቀረበውና ገራፊው ገብረየስ ጅሉ ሞሮን፤ “ዕድሜ ለእኔ በል፣ እሥር ቤት ውስጥ እኔ ስገርፍ እያየህ ከአንድ እስከ አርባ ቁጥር ተማርክ” የሚለውን ምፀታዊ አነጋገር ዕውን ከማድረግ የማይተናነስ ስህተት እንፈፅማለን፡፡ ከዚህ ይሰውረን!

Read 8718 times