የዋንጫ ፉክክሩ በማንችስተር ከተማዎቹ ክለቦች ሲቲ እና ዩናይትድ ተወስኖ በነገ ሁለት ወሳኝ ጨዋታዎች በግብ ልዩነት ሲለይ ከ44 ዓመት በኋላ የሊግ ሻምፒዮን ሊሆን የሚችለው ማን ሲቲ ሊነግስበት ይችላል፡፡ የእግር ኳስ ነገር ባይታወቅም ማን ዩናይትድም ሲቲ ከተሸነፈለት ወይም ከ10 በላይ ጎሎች ሰንደርላንድ ላይ አግብቶ 20ኛውን የዋንጫ ክብር ሊያገኝም ችሏል፡፡ ከአውሮፓ አምስት ታላቅ ሊጎች በታላቅነት መሪነቱን በይበልጥ የሚተናነቁት የእንግሊዙ ፕሪሚዬርሊግና የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ በመጨረሻ ሳምንት 18 ጨዋታዎች ነገ የውድድር ዘመኑን ያጠናቅቃሉ፡፡
የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ 10 ወሳኝ ጨዋታዎች ሻምፒዮናውን የሚወስኑ፤ የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳታፊዎችን የሚለዩና ወራጆችን የሚያሳውቁ በመሆናቸው ይጠበቃሉ፡፡
ከ10ሩ ጨዋታዎች የማንችስተር ከተማ ክለቦች ከሚኖራቸው ፍጥጫ ባሻገር ለሻምፒዮንስ ሊግ በቀረው የሁለት የቅድመ ማጣርያ ኮታዎች እድል ላይ ደግሞ አርሰናል፤ ኒውካስትል በሚያደርጓቸው ጨዋታዎች የገቡት ትንቅንቅ ትኩረት ይስባል፡፡ማንችስተር ሲቲ የሚከተለውን የዝውውር ፖሊሲ የተቃወመ አስተያየት ሰሞኑን የተናገሩት ሰር አሌክስ ፈርጉሠን የፋይናንስ እንቅስቃሴው በአውሮፓ እግር ኳስ ተመርምሮ እኩልነት መስፈን አለበት ብለዋል፡፡ ፈርጉሠን ሲቲ በተጨዋቾች የደሞዝ ክፍያና በዝውውር ገበያው የበላይነት ሊጉን መቆጣጠሩ ስፖርታዊ ጨዋነት አይደለም ይላሉ፡፡ ማን.ሲቲ በውድድር ዘመኑ ለተጨዋቾች በደሞዝ ብቻ ከ174 ቢሊዮን ፓውንድ በላይ ያወጣ ሲሆን ባለፉት 4 ዓመታት የክለቡ ባለሀብቶች በተጨዋቾች ግዢ ብቻ 450 ቢሊዮን ፓውንድ አውጥተዋል፡፡ ክለቡን የአቡዳቢው ባለሀብት ሼክ መንሱር በበላይነት ከያዙት በኋላ በመጀመሪያ የውድድር ዘመን 10ኛ ደረጃ፣ በ2ኛ የውድድር ዘመን 5ኛ ደረጃ፣ በ3ኛው የውድድር ዘመን ከ35 ዓመት በኋላ የኤፍካፕ ዋንጫ እንዲሁም በታሪክ የመጀመሪያው በሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ያገኘ ሲሆን፤ በሊግ ውድድር 3ተኛ ደረጃ ይዞ አጠናቋል፡፡ ዘንድሮ ደግሞ ከ44 ዓመታት በኋላ ሻምፒዮን ለመሆን ከጫፍ ደርሷል፡፡ የግሌዘር ቤተሰቦች ማን ዩናይትድን ከገዙ ባለፉት 7ዓመታት በትኬት ዋጋ ጭማሪና በቲቪ ስርጭት የተገኘ 500 ሚሊዮን ፓውንድ መሰብሰባቸውን ጋርዲያን ዘግቦታል፡፡ የአቡዳቢ ንጉሳዊ ቤተሰቦች በሲቲ ባለፈው 4 ዓመት ያወጡት ኢንቨስትመንት 1 ቢሊዮን ፓውንድ ደርሷል፡፡ ሮማን አብራሞቪችም ቢሆን በቼልሲ ቆይታቸው እስከ 2 ቢሊዮን ፓውንድ ፈሰስ አድርገዋል፡፡