Thursday, 18 October 2018 00:00

በዛምቢያ 1.6 ሚ. ዶላር የዘረፉ 80 ባለስልጣናት ከስራ ታገዱ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 የዛምቢያ መንግስት በአገሪቱ የትምህርት ሚኒስቴር ውስጥ በተፈጸመ የ1.6 ሚሊዮን ዶላር ዝርፊያ ላይ ተሳትፈዋል ያላቸውን ከ80 በላይ ባለስልጣናት ከስራ ማገዱን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ የትምህርት ሚኒስትር ቪንሰንት ሙዋሌ፤ ተዘርፏል ከተባለው የህዝብ ገንዘብ ጋር በተያያዘ ባለፈው ረቡዕ ለፓርላማ ባቀረቡት ሪፖርት፣ ባልተገባ የፋይናንስ አሰራር ዝርፊያው እንዲፈጸም አድርገዋል የተባሉ ከ80 በላይ ባለስልጣናት ላልተወሰነ ጊዜ ከስራ ገበታቸው እንደታገዱና ጉዳዩ ተጣርቶ ወንጀለኞች ለህግ እንደሚቀርቡ አስታውቀዋል፡፡  
ለልማት የሰጠሁት እርዳታ ለባለስልጣናት የግል ጥቅም መዋሉ አበሳጭቶኛል ያለው የእንግሊዝ መንግስት፣ ጉዳዩ ተጣርቶ ዝርፊያውን የፈጸሙት ባለስልጣናት በህግ እስኪጠየቁና ከሙስና የጸዳ አሰራር እስኪቀየስ ድረስ በአለማቀፍ የልማት ክፍሉ በኩል ለዛምቢያ መንግስት ሲሰጥ ነበረውን እርዳታ ለጊዜው ማቋረጡን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
በዛምቢያ የህዝብን ገንዘብ እየዘረፉና እያጭበረበሩ ለግል ጥቅማቸው የሚያውሉ ባለስልጣናት ቁጥር እየተበራከተ ነው ያለው ቢቢሲ፤ ባለፈው ወር ላይም ለድሃ ዜጎች ድጋፍ የተመደበ 4.3 ሚሊዮን ዶላር ከታለመለት ጉዳይ ውጭ እንዲውል አድርገዋል የተባሉት የአገሪቱ የማህበረሰብ ልማትና ጡረታ ሚኒስትር ኢምሪን ካባናሺ፣ በፕሬዚዳንት ኤድጋር ሉንጉ ትዕዛዝ ከስራቸው መባረራቸውን አስታውሷል፡፡

Read 2996 times