Saturday, 20 October 2018 13:39

በአዲስ አበባ አመራር ላይ አሲረዋል ተብለው የታሰሩት ጠበቃ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ አምነስቲ አሳሰበ

Written by 
Rate this item
(11 votes)


    “አዲስ አበባ በልጆቿ መመራት አለባት” በሚል በአሁኑ የከተማዋ አመራር ላይ አሲረዋል ተብለው የታሰሩት የህግ ጠበቃና የሰብአዊ መብት ተከራካሪው አቶ ሄኖክ አክሊሉ፤ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ከእስር እንዲለቀቁ አምነስቲ ኢንተርናሽናል አሳሰበ፡፡
ጠበቃ ሄኖክ አክሊሉ እና ሌላው ታሳሪ አቶ ሚካኤል መላኩ መታሰር፤ አሁንም በሀገሪቱ መሰረታዊ የሰብአዊ መብቶች ተሟልተው እየተከበሩ እንዳልሆነ ጉልህ ማሳያ ነው ብሏል የሰብአዊ መብት ተቋሙ፡፡
“እስሩ መንግስት የጀመረውን የፖለቲካ ምህዳር ማስፋት እንቅስቃሴን በእጅጉ የሚጎዳ ነው” ያለው አምነስቲ፤ “ፖሊስ የመብት ተሟጋቾችን ከማሰር ይልቅ መብታቸውን ሙሉ ለሙሉ የሚጠቀሙበትን አስቻይ ሁኔታ መፍጠር ይገባዋል” ብሏል፡፡
በሀገሪቱ ሃሳብን የመግለፅና የመደራጀት መብት ተሟልቶ እንዲከበር መንግስት ያለውን ቀናኢነት ሁለቱን ግለሰቦች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ከእስር በመፍታት ማሳየት አለበት ብሏል - አምነስቲ ኢንተርናሽናል፡፡
ለበርካታ የሽብር ተከሳሾች በነፃ ጭምር ጥብቅና በመቆም የሚታወቁት የህግ ባለሙያና ጠበቃ ሄኖክ አክሊሉ፤ “አዲስ አበባ በልጆቿ ብቻ ነው መመራት ያለባት” ሲሉ አሲረዋል በሚል ተጠርጥረው መታሰራቸውን ፖሊስ ለፍ/ቤት አስታውቋል፡፡
ረቡዕ እለት በፖሊስ ተይዘው የታሰሩት ተጠርጣሪው፤ ሐሙስ ፍ/ቤት የቀረቡ ሲሆን “የክፍለ ሃገር ልጅ አዲስ አበባን ሊመራ አይገባም” በሚል ወጣቶችን በመቀስቀስና በማደራጀት፣ እንዲሁም ከፍልስጤም ኤምባሲ ጋር ግንኙነት በመፍጠርና ስልጠና ወስደዋል በሚል መታሰራቸውን ፖሊስ ለፍ/ቤቱ አመልክቷል፡፡
ከህግ ባለሙያውና ጠበቃው አቶ ሄኖክ አክሊሉ ጋር የታሰሩት አቶ ሚካኤል መላኩም፤ በተመሳሳይ ድርጊት መጠርጠራቸውን ፖሊስ ለፍ/ቤቱ አስረድቷል። በተጠርጣሪዎች ላይ ተጨማሪ ማስረጃ ለማሰባሰብ ፖሊስ ተጨማሪ የ7 ቀን የምርመራ ጊዜ ተፈቅዶለታል፡፡

Read 6539 times