በአለማችን የተለያዩ አገራት በድምሩ 150.8 ሚሊዮን ያህል ህጻናት በተመጣጠነ ምግብ እጥረት ሳቢያ የሚከሰት የመቀንጨር ችግር ተጠቂዎች መሆናቸውንና ተጨማሪ 50.5 ሚሊዮን ህጻናትም የሰውነት ክብደታቸው ከሚገባው በታች መሆኑን አንድ አለማቀፍ ሪፖርት አስታውቋል፡፡ከትናንት በስቲያ የወጣው አለማቀፍ የስነምግብ ሪፖርትን ጠቅሶ አልጀዚራ እንደዘገበው፤ የህጻናት መቀንጨር በሁሉም የአለማችን አገራት የሚታይ ችግር ቢሆንም ከአለማችን አገራት በርካታ ቁጥር ያላቸው ህጻናት የችግሩ ሰለባ የሆኑባት ቀዳሚዋ አገር ህንድ ናት፡፡
የመቀንጨር ችግር ሰለባ ከሆኑት የአለማችን ህጻናት ከ35 በመቶ በላይ የሚሆኑት በህንድ እንደሚገኙ የጠቆመው ሪፖርቱ፤ በአገሪቱ 46.6 ሚሊዮን ህጻናት የመቀንጨር ችግር ሰለቦች መሆናቸውንና ተጨማሪ 25.5 ሚሊዮን ህጻናትም ከቁመታቸው አንጻር ተገቢው የሰውነት ክብደት እንደሌላቸው አመልክቷል፡፡በ140 የአለማችን አገራት ላይ የተሰራውን ጥናት መሰረት አድርጎ ይፋ የተደረገው ሪፖርቱ፣ የመቀንጨር ችግር ድሃ አገራትን ብቻ ሳይሆን ያደጉ አገራትንም ጭምር እያጠቃ እንደሚገኝና አለማችን በመቀንጨር ችግር ሳቢያ በየአመቱ 3.5 ትሪሊዮን ዶላር ያህል እንደምታጣም አክሎ ገልጧል፡፡