Print this page
Saturday, 12 January 2019 14:15

በጎንደር የንፁሃን ህይወትን ያጠፉ በህግ ይጠየቃሉ ተባለ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(5 votes)

 በአማራ ክልል ምዕራብ ጎንደር በገንዳ ውሃ ከተማ ከፀጥታ ኃይሎች ጋር በተፈጠረ ግጭት ህፃናትን ጨምሮ 8 ሰዎች የሞቱበትን ሁኔታ የሚያጣራ ቡድን ወደ ሥፍራው እንደሚላክ የገለፀው የአማራ ክልል መንግስት፤ ያልተመጣጠነ ኃይል የተጠቀሙ በህግ ይጠየቃሉ ብሏል፡፡
በአካባቢው በመንገድ ሥራ ፕሮጀክት ላይ ተሰማርቶ የነበረው ሱር ኮንስትራክሽን ድርጅት፣ ተሽከርካሪዎቹን ለማንቀሳቀስ በሞከረበት ወቅት በተፈጠረ አለመግባባት ክስተቱ መፈጠሩን የጠቆሙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው፤ በግጭቱ የንፁሃን ህይወት መጥፋቱ እንዳሳዘናቸው ተናግረዋል፡፡
የኮንስትራክሽን ድርጅቱን ከአካባቢው የፀጥታ ሁኔታ አንፃር መከላከያ ሰራዊት አጅቦት መጓዙ ተገቢ እንደነበር የጠቀሱት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ የተፈጠረው ሁኔታ ግን መሆን ያልነበረበት ነው ብለዋል፡፡ ችግር እንኳ ቢያጋጥም በትዕግስትና በውይይት ጉዳዩን ለመፍታት ጥረት ማድረግ ይገባ እንደነበርም ገልፀዋል፡፡
በቀጣይ የጉዳቱ ዝርዝር ተጣርቶ፣ ያልተገባና ተመጣጣኝ ያልሆነ እርምጃ የወሰዱ አካላት በህግ እንደሚጠየቁ አቶ ገዱ አስታውቀዋል፡፡
በገንዳ ውሃና በኮኪት ቀበሌ ላይ ላጋጠመው አደጋ መነሻ ምክንያቶቹን ያብራሩት የክልሉ የፀጥታና ደህንነት ኃላፊ ብ/ጀነራል አሳምነው ፅጌ፤ ህዝብ ሱር ኮንስትራክሽን የተባለውን ኩባንያ መሳሪያ አቀባባይና አስታጣቂ ነው ብሎ በመጠራጠሩ፣ ከአካባቢው ለመውጣት እንቅስቃሴ ሲጀምሩ እንዲፈተሽ መጠየቁንና ኩባንያው ግን ፍቃደኛ ሳይሆን መቅረቱን ጠቁመው፤ በዚህ መሃልም ተኩስ መፈጠሩንና መከላከያ ሰራዊትም ተመጣጣኝ ባልሆነ መሳሪያ በመተኮስ ምላሽ መስጠቱን ተናግረዋል፡፡
የጦር ኃይሎች ም/ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጀነራል ብርሃኑ ጁላ በበኩላቸው፤ መከላከያ ሰራዊት ፈፅሞ ወደ ህዝብ እንደማይተኩስ በመግልፅ፤ ተኩስ ሲከፈትበት ራሱን ለመከላከል ወደ ሰማይ ነው የተኮሰው ብለዋል፡፡ በቀጣይም በጉዳዩ ላይ ዝርዝር ማጣራት እንደሚደረግበትም አስገንዝበዋል፡፡  
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ባወጣው መግለጫ፤ ላይ የጦር ሃይሎች ጠቅላይ አዛዥ፣ የመከላከያ ሚኒስትርና ኢታማዦር ሹሙ በጉዳዩ ላይ ግልጽ ማብራሪያ እንዲሰጡ የጠየቀ ሲሆን ነፍስ አጥፊዎች በህግ እንዲጠየቁ፣ ተጐጂዎችም እንዲካሱ አሳስቧል፡፡
የመከላከያ ሠራዊት፤ የክልሉ መንግስት ባልጠየቀበት ሁኔታ፣ በተራ ደንብ ማስከበር ስራ ከመሠማራት ተቆጥቦ፣ ወደ ካምፑ እንዲሰባሰብና ሠላማዊ ህዝብን ከማሸበር ድርጊቱ እንዲቆጠብ እጠይቃለሁ ብሏል አብን፡፡
በሌላ በኩል በአካባቢው ቅማንት፣ አማራ በሚል ክፍፍል መሳሪያ የታጠቁ ወገኖች እርስ በርስ እየተገዳደሉ መሆኑን የገለፀው የክልሉ መንግስት፣ እነዚህ ግጭቶች እስካሁንም አለመቆማቸውን አስታውቋል፡፡
የእርስ በእርስ መገዳደሉ አላማቢስና መድረሻ የሌለው ነው ያሉት የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር ንፁሃኑን የአማራንና የቅማንት ህዝብ ለአደጋ ያጋለጠ አደገኛ አካሄድ በመሆኑ በአስቸኳይ መቆም አለበት ብለዋል፡፡
ከሁለቱም ወገን የታጠቁ ኃይሎች በአስቸኳይ ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ ያስጠነቀቁት አቶ ገዱ፤ አጥፊዎች ለህግ እንዲቀርቡም ህብረተሰቡ እንዲተባበር ጥሪ አቅርበዋል፡፡

Read 8114 times