Monday, 28 January 2019 00:00

ጆሃንስበርግ የአፍሪካ እጅግ ሃብታም ከተማ ተባለች

Written by 
Rate this item
(4 votes)

 አፍሪኤዥያ ባንክ፣ የ2018 የአፍሪካ ቀዳሚ አስር ሃብታም ከተሞችን ዝርዝር በቅርቡ ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ አጠቃላይ ሃብቷ 276 ቢሊዮን ዶላር የደረሰው የደቡብ አፍሪካዋ ጆሃንስበርግ በአንደኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡
ተቋሙ በአፍሪካ 23 ከተሞች የሃብት መጠን ላይ ያደረገውን ጥናት መሰረት አድርጎ ባወጣው ሪፖርት መሰረት፣ ሌላኛዋ የደቡብ አፍሪካ ከተማ ኬፕታውን፣ በ155 ቢሊዮን ዶላር አጠቃላይ ሃብት፣ የሁለተኛነት ደረጃን የያዘች ሲሆን የግብጽ መዲና ካይሮ በበኩሏ፣ በ140 ቢሊዮን ዶላር አጠቃላይ ሃብት፣ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡
የናይጀሪያዋ ሌጎስ በ108 ሚሊዮን ዶላር፣ የደቡብ አፍሪካዋ ደርባን በ55 ቢሊዮን ዶላር፣ የኬንያ ርዕሰ መዲና ናይሮቢ በ54 ቢሊዮን ዶላር፣ ሉዋንዳ በ49 ቢሊዮን ዶላር፣ ፕሪቶሪያ በ48 ሚሊዮን ዶላር፣ ካዛብላንካ በ42 ቢሊዮን ዶላር እንዲሁም የጋና ዋና ከተማ አክራ በ38 ቢሊዮን ዶላር እንደ ቅደም ተከተላቸው ከአራተኛ እስከ አስረኛ ያለውን የሃብት ደረጃ መያዛቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡
በሌላ የተቋሙ ጥናት ደግሞ፣ በአፍሪካ አህጉር የግለሰቦች ሃብት አጠቃላይ ድምር በአመቱ 2.3 ትሪሊዮን ዶላር የደረሰ ሲሆን ይህ የሃብት መጠን በመጪዎቹ አስር አመታት ጊዜ ውስጥ የ34 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 3.1 ትሪሊዮን ዶላር ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅም ተመልክቷል፡፡

Read 6090 times