Monday, 28 January 2019 00:00

”አብራክ” ልብወለድን እንዳነበብኩት

Written by  መርስዔ ኪዳን ከሜኔሶታ፤ ሃገረ አሜሪካ
Rate this item
(0 votes)


    “አብራክ” የተባለውን የደራሲ ሙሉጌታ አረጋዊ መጽሐፍ አነበብኩት። አገራችን ከሊቅ እስከ ደቂቅ በዘውጌ ብሄርተኝነት ተጠፍሮ ከዘውጉ፣ ወይ ከብሄሩ፣ ወይ ከጎሳው አሻግሮ ማሰብና ማለም ባልቻለበት በዚህ ወቅት፣ ለንባብ መብቃቱ በጣም ጠቃሚ ሆኖ አግኝቸዋለሁ።
“አብራክ” አርካኒ ጫላ በተባለች ኦሮሞ ኢትዮጵያዊትና ዋልታ ሐጎስ በተባለ ትግሬ ኢትዮጵያዊ መካከል ያለውን የፍቅር ግንኙነት ተመርኩዞ፣ በአሁኑ ወቅት በአገራችን የገነነውን የብሄርተኝነት ፖለቲካ አስከፊ ገጽታ ያሳየናል። “አብራክ” በአርካኒና በዋልታ ዙሪያ ያሉ ቤተሰቦቻቸውን፣ ጓደኞቻቸውን፣ ዘመዶቻቸውን፣ የስራ አለቆቻቸውንና ሰራተኞቻቸውን ጭምር በመጠቀም በአገሪቷ ውስጥ ያለውን ስር የሰደደ ብሄርተኝነትና የስርአት ብልሹነት ፍንትው አድርጎ ያሳያል።
“አብራክ”ን ስታነብ
የዋልታ እናት ወ/ሮ ጽጌ፤ እውነተኞቹን ለነፃነትና ለእኩልነት የታገሉ ነገር ግን፣ ያ የታገሉለት የነፃነትና የእኩልነት አላማ በራስ ወዳዶችና በጭፍን ካድሬዎች ተቀልብሶ ህዝብ ሲበደልና አገር ስትታመስ እያዩ የሚብሰከሰኩ የህወሓት ታጋዮችን ወክላ ስትታመም አብረሃት ትታመማለህ፣ ስትቆጭ አብረሃት ትቆጫለህ፣ ስትታሰር አብረህ ትታሰራለህ።
የአርከኒ አባት አቶ ጫላ ባንድ በኩል በወንድማቸው በአቶ ታዬ ግፊት እንዲሁም በሚኖሩበት በአምቦ ከተማ የመንግስት ባለስልጣናት፣ ህዝቡ ላይ በሚፈጽሙት ወከባና በደል፣ ወደ አክራሪ ኦሮሞ ብሄርተኝነት ሲጎትታቸው፣ በሌላ በኩል ደግሞ ያሳለፉት ረጅም የስራ ልምድና በትምህርት ያገኙት እውቀት ላይ የልጆቻቸውና ዘመናዊ አስተሳሰብ ተጨምሮ ወደ አመክንዮ ሲጎትታቸው፣ አንባቢውም አብሯቸው ይዋልላል፡፡  
የዋርካ ወንድም አቶ ክብረት፤ እቺን ሃገር ብዙ ሺህ ወጣቶችን መስዋእት አድርጎ፣ የመንግስት ስልጣንን ከተቆጣጠረው ድርጅት ውጪ ሌላ ሊመራት የማይችል የሚመስላቸው፣ በድርጅቱ ርእዮት ተወልደው፣ በድርጅቱ ፕሮፓጋንዳ ተጠምቀው፣ በድርጅቱ ፍፁም ታማኝ አባልነት የጎለመሱ፣ ከድርጅቱ ውጪ ያለ ሁሉ ጠላት የሚመስላቸው የደነዘዙ የህወሓት ካድሬዎችን ወክሎ ባንድ በኩል፣ ወንድሙንና እናቱን ሳይቀር ህዝብን ሲያንገላታ፣ በሌላ በኩል ራሱ ለፍቶ በገነባው የድርጅት መዋቅር፣ እስረኛ ሆኖ ሲንገላታ እያነበብክ፣ ተበሳጭተህበት እንደገና ታዝንለታለህ።
የዋልታና የክብረት እህት መብራት ደግሞ በድርጅቱ የፕሮፓጋንዳ ጫና እንዲሁም ድርጅቱ እያንዳንዱ ግለሰብን በሚያስገድድበት ማህበረሰባዊ ጫና፣ በገፍ ወደ አባልነት የገቡትን ለአለቆቻቸው ፍፁም ታዛዥና ተገዢ፣ ለበታቾቻቸው ጨካኝ አለቃ፣ ለህዝብ ደግሞ ሰይጣንን እንኳ በሚያስንቅ መጠን ጭካኔና ጋጠ-ወጥነት የሚያሳዩ፣ የድል አጥቢያ አርበኛ ካድሬዎችን ወክላ፣ በተለይ የህወሓት ካድሬዎች በትግራይ ህዝብ ላይ የሚያደርሱትን አስከፊ በደል ታሳይሃለች። የድርጅቱ ካድሬዎች በፕሮፓጋንዳና ግምገማ ደንዝዘው፣ ሰብአዊነታቸውን አጥተው፣ ህዝቡን ሲያንገላቱ፣ በገነቡት የአፈና መዋቅር መልሰው ራሳቸው ሲንገላቱ አንብበህ፣ በጣም ታዝንባቸዋለህ፤ መልሰህ ደግሞ ታዝንላቸዋለህ።
የዋሁና ለጋሱ የአርካኒ አጎት አቶ ታዬ፤ ስርአቱንና የትግራይን ህዝብ ሳይለይ፣ በትግሬ ጥላቻ ሲናውዝ፣ ጋዜጠኛው ሞቲ ሃሳቡን በመግለፁ ብቻ በሚጠላው ፖለቲከኛነት ተከሶ ለእስር ሲዳረግ፣ ሰለሞን የተባለው ሃቀኛ የህወሓት ባለስልጣን ራስ ወዳድና ጭፍን ባልደረቦቹ ህዝቡ ላይ የሚያደርሱት በደል እያሳዘነው ነገር ግን ያለውን ሁኔታ ለመቀየር ሊያደርገው የሚችለው ነገር ባለመኖሩ ተስፋ ቆርጦ ሲብከነከን፣ ከመሬታቸው ተፈናቅለው በገዛ መሬታቸው ላይ በተሰራ ቤት በዘበኝነት የተቀጠሩት የዋልታ ዘበኛ፣ ከትግራይ መጥተው በአርካኒና በኦብሴ ቤት፣ በቤት ሰራተኝነት የተቀጠሩት ሴቶች፣ የዋልታ ጓደኛ በቀለና ሌሎች ገፀባህሪያት በሚያደርጉት መስተጋብር፣ በህዝቡ ውስጥ ያለውን የተለያየ አስተሳሰብ ትቃኛለህ፡፡
ደራሲው ሙሉጌታ አረጋዊ፤ በ”አብራክ” ውስጥ በወቅቱ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ  ፍንትው አድርጎ አሳይቶናል። እንደ ሀዲስ አለማየሁ፣ የዛሬ ችግራችንን ዛሬ ነግሮናል። እንደ በዓሉ ግርማ፣ በራሱ ህይወት ዙሪያ የራሱን እይታ ተርኮልናል። ነገር ግን ድርሰቱ በሀዲስና በበዓሉ ድርሰቶች ውስጥ የምናየው ስዕላዊነት ይጎድለዋል። በመጀመሪያው ገፆች ላይ የአርካኒ ወላጆችን ቤት በጥሩ ስዕላዊ አገላለፅ የሳለልን ሲሆን ከዚያ በኋላ ያሉትን መቼቶች በቅጡ አልሳላቸውም። ከአምቦ ከተማ በስተቀር ሌሎች ከተሞችን እንደ ግኡዝ አካል ስማቸውን ከመጥቀስ በስተቀር ህያው ባህሪያቸውን አልተረከልንም። ለምሳሌ መቀሌ በድርሰቱ ውስጥ የትርክቱ  ዋነኛ አካል ብትሆንም፣ የመቀሌን ታሪክ፣ መልክአምድር እንዲሁም የነዋሪዎቿን ባህልና አኗኗር በቅጡ አልሳለልንም። በተለይም የህዝቧን ሰው አፍቃሪነትና እንግዳ አክባሪነት ሳይተርክ ማለፉ፣ መቀሌን ለሚያውቃት ሰው አይዋጥለትም።
በአክራሪ ብሄርተኝነት ተለክፈን እርስ በርስ በምንራኮትበት በዚህ ወቅት፣ የዚህች መፅሐፍ ለአንባቢ መድረስ በጣም አስፈላጊ ነው። አንድ ወዳጄ፤ የአስቴር አወቀ የፍቅር ዘፈኖች፣ ፍቅር ለያዛቸው ሰዎች መድሃኒት ይሆን ዘንድ በየመድሃኒት ቤቱ መሸጥ አለበት ይለኝ ነበር፡፡ እኔ ደግሞ አክራሪ ብሄርተኝነት የተጠናወታቸው ሰዎች “አብራክ”ን አንብበው ይፈወሱ እላለሁ።
መጽሐፉ በነሐሴ 2018 በዋሺንግተን ዲሲ ለመጀመሪያ ጊዜ የታተመ ሲሆን በታህሳስ 2018 በአዲስ አበባ እንደገና ታትሟል፡፡ በ453 ገጾች የተቀነበበው “አብራክ”፤በ220 ብር እየተሸጠ ነው፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጸሃፊውን በኢሜይል አድራሻው This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. ማግኘት ይቻላል፡፡

Read 1198 times