Thursday, 07 February 2019 00:00

300 ፕሮፌሰሮች፤ አልበሽር በአፋጣኝ ስልጣን እንዲለቁ ጠየቁ

Written by 
Rate this item
(4 votes)


    በሱዳን መንግስት ላይ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ተባብሶ የቀጠለ ሲሆን በዩኒቨርሲቲ ኦፍ ካርቱም የሚያስተምሩ 300 ፕሮፌሰሮችና ከ200 በላይ የዩኒቨርሲቲው መምህራንና ሰራተኞች ባለፈው ረቡዕ ባደረጉት ተቃውሞ፤ ፕሬዚዳንት ኦማር አልበሽር በአፋጣኝ ስልጣን እንዲለቁ መጠየቃቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
በአገሪቱ አንጋፋው እንደሆነ በሚነገርለት የካርቱም ዩኒቨርሲቲ ቅጽር ግቢ ውስጥ ባለፈው ረቡዕ በተከናወነው ሰላማዊ ሰልፍ፤በፕሬዚዳንቱ ላይ ያላቸውን ተቃውሞ የገለጹት የዩኒቨርሲቲው ፕሮፌሰሮችና መምህራን ባወጡት የጋራ መግለጫ፤ ለሶስት አስርት አመታት አገሪቱን ያስተዳደሩትና ህዝቡን ለከፋ ኑሮ የዳረጉት ፕሬዚዳንት አልበሽር፣ በአፋጣኝ ስልጣን እንዲለቁና የሽግግር መንግስት እንዲቋቋም ጠይቀዋል፡፡
በሱዳን ፕሮፌሽናሎች ማህበር አስተባባሪነት የተካሄደው የተቃውሞ ትዕይንት፤እስካሁን ድረስ በአገሪቱ ከተደረጉት ተቃውሞዎች ሁሉ ተጽዕኖ የመፍጠር አቅሙ ከፍ ያለ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ ላለፉት ስድስት ሳምንታት ያህል ተቃውሞ በርትቶባቸው የቆዩትን አልበሽር፤ አደጋ ውስጥ ይጥላቸዋል ተብሎ መሰጋቱን አመልክቷል፡፡
በሱዳን ተባብሶ በቀጠለው ተቃውሞ እስካሁን ድረስ 40 ያህል ሰዎች ለሞት መዳረጋቸው መነገሩን የጠቆመው ዘገባው፤ የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችን፣ አክቲቪስቶችንና ጋዜጠኞችን ጨምሮ ከ1 ሺህ በላይ ሰዎች መታሰራቸውንም ገልጧል፡፡
የአገሪቱ ብሔራዊ የስለላና የደህንነት አገልግሎት ተቋም ባለፈው ማክሰኞ ከተቃውሞው ጋር በተያያዘ የታሰሩ ዜጎች በሙሉ እንዲፈቱ ውሳኔ ማሳለፉን ያስታወሰው ዘገባው፤ የተፈቱ እስረኞች ስለመኖራቸው እስካሁን የታወቀ ነገር የለም ብሏል፡፡

Read 4671 times