ስራ ፈትተው በየማህበራዊ ድረገጹ የሆነ ያልሆነውን ሲለጥፉ የሚውሉ ዜጎችን ላለማበረታታትና በዚያውም ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት በሚል ከወራት በፊት በኢንተርኔት አገልግሎት ተጠቃሚዎች ላይ አዲስ ግብር የጣለቺው ኡጋንዳ፣ በግብሩ የተማረሩ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች፣ ኢንተርኔት መጠቀም ማቆማቸው ኢኮኖሚዋን ስጋት ላይ እንደጣለው ተዘግቧል፡፡
የኡጋንዳ መንግስት ባለፈው ሃምሌ ወር ላይ ተግባራዊ ያደረገውና በአንድ ቀን 4 ፓውንድ ያህል የሚደርሰው የኢንተርኔት ግብር ያማረራቸው 2.5 ሚሊዮን ያህል የአገሪቱ ዜጎች ኢንተርኔት መጠቀም ማቆማቸውን የዘገበው ዘ ጋርዲያን፣ ይህ አዝማሚያ ከቀጠለ መንግስት ከኢንተርኔት ያገኝ የነበረውን ከፍተኛ ገቢ እንደሚያሳጣውና የአገሪቱን ኢኮኖሚ ሊጎዳው እንደሚችል መሰጋቱን አመልክቷል፡፡
የኢንተርኔት ግብሩ በተለይም የሞባይል ኢንተርኔት ተጠቃሚዎችን ቁጥር በእጅጉ እንዲቀንስ ማድረጉን የጠቆመው ዘገባው፣ አገሪቱ ከሞባይል የገንዘብ ዝውውር አገልግሎቶች ታገኘው የነበረው ገቢ ብቻ በቴክኖሎጂው ይዘዋወር የነበረው የገንዘብ መጠን ከሰኔ እስከ መስከረም በነበሩት ወራት በሩብ ያህል በመቀነስ፣ 3.4 ቢሊዮን ፓውንድ መድረሱንም አስታውሷል፡፡
Published in
ከአለም ዙሪያ