Print this page
Saturday, 27 April 2019 10:11

በሀሳብ መንገድ ላይ

Written by  ተመስገን
Rate this item
(4 votes)


                            “እግዜርን ምክንያትንና ዕውቀትን መለያየት አይቻልም”
                             
              ብዙ የክርስቲያን ሊቃውንት “እግዜር መልክ የለውም፤ ቢኖረው እንኳ መልከ ብዙ ወይም ሁሉ ነገሩ መልክ ስለሆነ ከሰው በስተቀር አምሳያው አይለይም፤ ተፈጥሮ አንዷ ገፁ ናት፡፡” ይላሉ፡፡ ተፈጥሮ የምትመራውም ሆነ የምትተዳደረው በራሷ ህግና ስርዓት ነው፡፡ ህግና ስርዓቷም (Law and order of nature) እንዲሉ የሚመለከው ከምክንያት የተወለደ በመሆኑ ነው ባይ ናቸው፡፡
ሰው ግን በዚህ ጉዳይ ይለያል፡፡ አንዳንድ ጊዜ እግዜርና ሰው ተዋህደው በምክንያትም በአካልም አንድ ይሆናሉና!! እንደ ግለሰብ (One entity) አእምሮና ልብ ዕኩል ሲመዝኑ፣ ዕኩል ምክንያታዊ ሲሆኑና ተመሳሳይ position በሚኖራቸው ጊዜ እግዜር ሰውዬውን፣ ሰውየውም እግዜርን ይሆናል፡፡ እዚህ ጋ ሰው “በአምሳሉ ተፈጠረ” ይሰኛል፡፡ … “To be good is to be God!!” እንዲሉ፡፡ …
እንዲህ ባልሆነበት ጊዜ ግን ግለሰቡ ውስጥ የሚፈነጨው ተቃራኒው መንፈስ ስለሆነ ‹ሰው› የመሆን ቅድስናው ይረክሳል፡፡ ምክንያታዊነቱ ይደበዝዛል፡፡ ይህን ተቃራኒ መንፈስ ለማባረርና የነፍሱን መንበር ለማፅዳት በተለያየ መንገድ ራሱን ይፈትናል፡፡ ፆም፣ ፀሎት፣ ሱባኤና በመሳሰሉት አካሉንና መንፈሱን ይገራል፡፡ አንዳንዶች ገላቸውን በእሾህና በአለብላቢት በመጠብጠብ ራሳቸውን ይቀጣሉ … ክርስቶስ የተቀበለውን ፍዳ ለማስታወስ:: … አብረውት ተሰቃይተው፣ አብረውት ሞተው፣ አብረውት ይነሳሉ … እናም ፋሲካ ይሆናል፡፡
እንኳን አደረሳችሁ!!
***
የእግዜር ዘላለማዊ ፀጋ በሁሉም ነገር ላይ ይታያል፡፡ በሰው አእምሮ ላይ ደግሞ ይበዛል:: ከሁሉም በላይ የተገለፀበት ግን በኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ The eternal wisdom of God … has shown itself forth in all things, but chifly in the mind of man, and most of all in Jessus Christ)” Spinoza  
ወዳጄ፡- “እግዜር በአንድ ሰው በኩል ሁሉም ህዝቦች በምድር ላይ ተንሰራፍተው እንዲኖሩ ፈቀደ … እሱም ከያንዳንዳቸው ጎን አልራቀም::”  ተብሎ በዘፍጥረት ቢጠቀስም፣ የሰው ልጅ በተሰጠው ፀጋ ሊጠቀም አልቻለም፡፡ እራሱን አጠበበ፣ በገዛ ቅዠቱ ተተበተበ፡፡ እርስ በርስ እየተጋጨ አጠገቡ የነበረውን ‹አምላክ› ገፋው:: የአስተሳሰብ መዘውር (regulator) ነው የሚባለውን ዕውቀት መፍለቂያ አእምሮውን ለቅድስና አላዋለውም፡፡ ፍሬዲሪክ ኒች የመጨረሻው ክርስቲያን በመስቀል ላይ ሞቷል (The last Christian died on the cross”) የሚለው ያለምክንያት አልነበረም፡፡ እግዜርን በየአደባባዩ ፈልጎ ባጣው ‹ዕብድ መሳይ› ፍጡ በኩልም፡-
“እውነትት እውነት እላችኋለሁ፡፡ እግዜር ሞቷል፣ አጠገባችን የለም፡፡ ካልሞተ ወዴት ሄደ? … እስኪ ንገሩኝ የገደልነው እኛው ነን፤ እኔና እናንተ::” በማለት መልካምነት የራቀን ምክንያታዊነትን በመግደላችን እንደሆነ ያስታውሰናል፡፡ መፋቀር ያለመቻል፣ ፍትሃዊ አለመሆን፣ አንድነት ማጣት… ከምን ይመነጫል ታዲያ? እያለም ያፋጥጠናል፡፡
ወዳጄ፡- እግዜር ርህሩህ እንደሆነ በዮናስና በነነዌ፣ በአብርሃምና በእስማኤል እንዲሁም ቁጥር ስፍር በሌላቸው አጋጣሚዎች ተስተውሏል፡፡ “ከፍጥረታት ሁሉ ሰውን በመፍጠሬ ተፀፅቻለሁ፣ ከምድር ገፅም እጠራርገዋለሁ (a’m going to wipe men whom I have created, because I do regret that I have made them, Genesis 6:1-8) በማለት የዛተበት ጊዜ እንደነበረም ተፅፏል፡፡
ወዳጄ፡- በዚህ ዘመን ከሳይንስና ከትርክት በተለየ መንገድ የተለያዩ የዕምነት ተቋማት እኛ “እግዜር” እያልን የምንጠራውን መንፈስ ለመግለፅ የሚጠቀሙበት የየራሳቸው የአስተሳሰብ ዘይቤ አላቸው፡፡ ክርስትና፤ የህይወት መንገድ ኢየሱስ ነው ሲል፤ እስልምና የህይወት መንገድ ለአላህ ራስን ማስገዛት (Submission) ነው ይላል፡፡ ለሂንዱኢዝም liberation ሲሆን ለቡድሂዝም የህይወት መንገድ ዕውቀት ወይም ኢንላይትመንት ነው፡፡ ለኮንፊዩሻኒዝምና ለጣዖኢዝም ደግሞ ‹Tao› ማለት በራሱ የህይወት መንገድ ማለት ነው፡፡ ለአይሁድ የህይወት መንገድ ጥንታዊ ስክሪፕቸርስንና የብሉይ መሰረቶችን ማወቅ ሲሆን ሌሎችም የየራሳቸው አመለካከት አላቸው፡፡
ፈረንሳዊው ፈላስፋና ሳይንቲስት ፓስካል ዋገር በክርስትና ሃይማኖት ከማመንና ካለማመን የሚገኘውን ጥቅም ሲያነፃፅር፡-
“በእግዜር ብናምንና መኖሩ ቢረጋገጥ መንግስተ ሰማያትን ወርሰን ዘለዓለማዊ ህይወት ይኖረናል፡፡ በእግዜር እያመንን ነገር ግን እሱ ባይኖር፣ የሚቀርብን ነገር እንደ “ሃጢአት” የምንቆጥራቸው ከልክ ያለፉ ፈንጠዝያዎችና ልቅነት (sinful pleasures) ነው፡፡ ይኸ መሆኑ ጥቅም እንጂ ጉዳት የለውም፡፡ በእግዜር ባናምንና መኖሩ ከተረጋገጠ ደግሞ መጨረሻችን ገሃነም ይሆናል፡፡ ባናምንበትና እሱም ከሌለ ግን ችግር የለም፡፡” በማለት ምርጫውን ለኛ ትቶልናል፡፡
ከብዙ ሳይንሳዊ አስተሳሰቦች ደግሞ አንዳንዶቹን እንደ ‹ጨዋታ› ብናነሳ ወይም እንደ ምሳሌ ብንወስድ፡- “እግዜር የተፈጠረው በሰዎች አእምሮ ውስጥ ነው … ከፍርሃት የተነሳ” ባይ አያሌ ናቸው፡፡ “ሰዎች የሚፈሩት አካል ወይም ሃይል ያስፈልጋቸዋል፣ እግዜር ባይኖራቸው ‹እግዜር› ፍጠሩላቸው (where there is no God create one”) በማለትም ይመክራሉ:: ይኸን አባባል እንደ ቮልቴርና ዶስተቭስኪ የመሳሰሉ ታላላቅ ጠቢባን ተጠቅመውበታል፡፡
ከ1856-1939 የኖረው ታላቁ ሳይኮአናሊስት ሲግመንድ ፍሮይድ “Totem and Taboo” በሚለው መጽሃፉ “ጥንታዊና ኋላ ቀር በነበረው ወይም የጭለማ ዘመን በሚባለው ጊዜ የነበሩት ያልለመዱና ያልተገሩ ፈረሶችና የቀንድ ከብቶች የሚከተሉትና በስሩ ሆኖ የሚግተለተለው መንጋ የሚለየው በትልቁ ወንድ ነበር - በጉልበተኛው:: ገና ከአውሬነት ባህሪ ባልተላቀቀው “የሰው ልጅ” ቤተሰብ ውስጥም አባት ወሳኝ ቦታ ነበረው፡፡ ያኔ ልጆቹን እየተጫነ የፈለገውን ማድረግ የሚችል ፈላጭ ቆራጭ እሱ ብቻ ነው፡፡ ልጆቹ በአንድ በኩል ሲያደንቁትና እሱን መሆን ሲመኙ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ስለሚፈሩትና ስለሚቀጣቸው ይጠሉታል፡፡ ጎርምሰው ጉልበት ባገኙ ጊዜ ግን ገደሉት፡፡ ኃይልና መንፈሱ እንዲዋሃዳቸውም ከስጋው በልተው ከደሙ ተጎነጩ፡፡ ነገር ግን በስራቸው በመፀፀታቸው፣ የአባታቸውን መንፈስ ይቅርታ ለመለመን በየጊዜው የተለያዩ ድርጊቶችን ማከናወን ጀመሩ፡፡
“ይኸም ድርጊታቸው ሲደጋገምና እየተወራረሰ ሲመጣ ወደ ስርዓተ አምልኮነት (rituals) ተሸጋገረ:: የመጀመሪያው አባታቸው መንፈስም “እግዜር” እየሆነ መጣ፡፡ የጎረሱት ስጋና የተጎነጩት ደምም በክርስትና እምነትና በአንዳንድ አምልኮዎች “ስጋ ወደሙ” እየተባለ የሚዘከረው ስርዓት መሰረት ሆነ” በማለት ያስነብበናል፡፡
በነገራችን ላይ ወዳጄ፡- “እግዜር፣ ምክንያትና ዕውቀትን መለያየት አይቻልም” የሚሉ ብዙ ናቸው:: … አንተስ ምን ትላለህ? እነሆ ምርቃት:-
“He who kills a man kills a reasonable creature in God’s image. But, he who destroys a good book destroys reason itself, God himself.”
ሠላም!!     

Read 1266 times