Saturday, 27 April 2019 11:02

ዳሽን ባንክ ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት አስተዋወቀ

Written by  መንግስቱ አበበ
Rate this item
(4 votes)


              ዳሽን ባንክ “ሽሪክ” በሚል ስያሜ  ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት ዙሪያ፤ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሴሚናር ባለፈው ሳምንት በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል የሰጠ ሲሆን የሸሪክ፣ የአንኒዳእ (ሴቶች) እና የሂባ (የስጦታ) የኤሌክትሮኒክስ ካርዶችን አስተዋውቋል።
ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት አሠራሩ እንደሌሎቹ የባንክ አገልግሎቶች የንግድ ግብይት ሂደት ብቻ ሳይሆን፣ የሸሪዓ መርሆዎች፣ ዕሴቶችና ህግጋትን ለመጠበቅ አኳያ ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሻ ዘርፍ በመሆኑ  የህግ፣ የሞራልና የተገቢነት ተጠየቆች መሟላታቸውን ለማረጋገጥ አገልግሎቱን ዘግይቶ መጀመሩን ባንኩ አስታውቋል፡፡
ለወለድ ነፃ ባንክ አገልግሎቱ የሽሪዓ እሴቶችን ሳያጓድል እየተከናወነ ለመሆኑ የሚከታተል፤ በማኀበረሰቡ ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት፤ ዕውቅናና አመኔታን ያተረፋ፣ በዘርፋ በቂ የትምህርት ዝግጅት ፣ዕውቀትና ልምድ ያላቸው አምስት የእምነቱ ሊቃውንት የሚገኙበት ገለልተኛ የሆነ ባለሙሉ ስልጣን የሸሪዓ አማካሪ ኮሚቴ በቋሚነት መድቦ ወደ ሥራ መገባቱን በሴሚናሩ ላይ ተብራርቷል፡፡
በእለቱ በወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎትና ፋይናንስ እንዲሁም በሸሪዓ-መርሖዎች ዙሪያ በዘርፋ ምሁራን ገለጻ የተደረገ ሲሆን ከታዳሚው ለተነሱ ጥያቄዎች በዳሸን ባንክ ከፍተኛ አመራሮችና በባንኩ የሸሪያ አማካሪ ኮሚቴ አባላት ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቷል::
ዳሸን ባንክ ከዚህ ቀደም መሰል ሴሚናሮችን በደሴ፣ ድሬዳዋ፣ ጅማ፣ አዳማ፣ወራቤና መቀሌ ከተሞች ያከናወነ ሲሆን  ከወለድ ነጻ  የባንክ አገልግሎት ከግንቦት 8 ቀን 2011 ዓ.ም ጀምሮ በሁሉም የባንኩ ቅርጫፎች ለአገልግሎቱ በተለዩ መስኮቶች መስጠት እንደሚጀምር አስታውቋል፡፡

Read 3963 times