Sunday, 16 June 2019 00:00

3ኛው ዙር “ጣና ሶሻል ሚዲያ አዋርድ” ጳጉሜ 1 ይካሄዳል

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(0 votes)

 በዘመራ መልቲ ሚዲያ አዘጋጅነት በየዓመቱ የሚካሄደውና ማህበራዊ ሚዲያን ለበጎ ተግባር የሚጠቀሙ ግለሰቦችንና ተቋማትን አወዳድሮ የሚሸልመው “ጣና ሶሻል ሚዲያ አዋርድ” ሶስተኛው ዙር ሽልማት፤ ጳጉሜ 1 ቀን 2011 ዓ.ም በባህር ዳር ይካሄዳል፡፡
የዘንድሮው ሽልማት የሚካሄደው እንደወትሮው በሆቴል ውስጥ ሳይሆን ከ1 ሺህ ሰው በላይ በምትይዘው ጣናነሽ ጀልባ በጣና ሀይቅ ላይ ጉዞ እየተደረገ መሆኑን የሽልማቱ አዘጋጅ የዘመራ መልቲ ሚዲያ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ደምስ አያሌው ገልፀዋል፡፡ ባለፉት ሁለት ዙሮች፣ በ16 ዘርፎች ተቋማትንና ግለሰቦችን ሲሸልም የነበረው ድርጅቱ፤ ዘንድሮ ስድስት አዳዲስ ዘርፎችን ጨምሮ ወደ 21 ዘርፎች ከፍ ማድረጉም ታውቋል፡፡
ዘርፎቹም “በተፅዕኖ ፈጣሪ ሴት”፣ “በፀረ ሙስናና ስነ ምግባር” “በጀማሪ የስነ ፅሁፍ ሰው”፣ “በፈጣን ወቅታዊና ሚዛናዊ መረጃ”፣ “በባህልና ቱሪዝም”፣ “በስፖርትና በታሪክ”፣ “በፎቶግራፍ፣ በጤና”፣ “በንግድና ቢዝነስ”፣ “በትምህርትና ማህበረሰብ አገልግሎት”፣ “በጥናትና ምርምር”፣ “በሳይንስና ቴክኖሎጂ”፣ “በበጎ አድራጎትና አካባቢ ልማት”፣ በቲዩብ ፈጣን፣ ወቅታዊና ሚዛናዊ መረጃ”፣ በ“ዩቲዩብ በብዛት የታየ የሙዚቃ ቪዲዮና ፊልም” በ“ስነ ጥበባዊ ምስሎችና ትርክቶች” ዘርፍ ሽልማቱ እንደሚካሄድ አቶ ደምስ አያሌው ገልፀው፣ የጣና ሶሻል ሚዲያ አዋርድ ሀሳብና ሎጎው ባለፈው የካቲት ከአዕምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት የፈጠራ መብት ባለቤትነት ፈቃድ ማግኘቱንም ጨምረው ገልፀዋል፡፡


Read 5422 times