ከአሜሪካ የተሰረቀውን ሚስጥራዊ ወታደራዊ መረጃ በድብቅ ለቻይና አሳልፎ ሰጥቷል የተባለው ቻይናዊ ፕሮፌሰር፤ በ200 አመታት እስር መቀጣቱን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
የኤሌክትሮኒክ የጦር መሳሪያዎችና የተዋጊ ጄቶች አፕሊኬሽኖችን እንደያዘ የተነገረለትን የኮምፒውተር ቺፕስ በድብቅ ወደ ቻይና ለመላክ በተደረገው እንቅስቃሴ ውስጥ ተሳትፏል በሚል ባለፈው አመት ጥር ወር ላይ በቁጥጥር ስር የዋለው ፕሮፌሰር ይሺ ሺሽ የራዳር፤ በቀረቡበት 18 ክሶች ሁሉ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ የ200 አመታት እስር እንደተፈረደበት ዘገባው አመልክቷል፡፡
ሎስ አንጀለስ ውስጥ በሚገኘው ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ካሊፎርኒያ፣ የኤሌክትሪካል ምህንድስና መምህር የሆነው የ64 አመቱ ፕሮፌሰር ይሺ ሺሽ፤ ከግብረ አበሮቹ ጋር በመሆን ይህንን እጅግ ፈጣንና ልዩ የኮምፒውተር ቺፕስ ቻይና ውስጥ ለሚገኝ አንድ ኩባንያ አሳልፎ በመስጠቱ ቅጣቱ እንደተጣለበት ተነግሯል፡፡
አገራዊ መረጃን አሳልፎ ከመስጠት ባለፈ የውጭ አገራት ኩባንያዎች ቴክኖሎጂውን ተጠቅመው የአሜሪካን ህልውና አደጋ ላይ የሚጥሉ አዳዲስ ወታደራዊ አፕሊኬሽኖችን የሚሰሩበትን ዕድል የሚከፍት አደገኛ ድርጊት ፈጽሟል የተባለው ፕሮፌሰሩ፤ ከዚህ በተጨማሪም የቻይና ኩባንያዎች የአሜሪካ ኩባንያዎችን ፈጠራዎችና ቴክኖሎጂዎች ተጠቅመው ያልተገባቸውን ጥቅም እንዲያገኙ የሚያደርግ ወንጀል ሰርቷል በሚል የእስር ፍርዱ እንደተወሰነባቸው ተገልጧል፡፡