Saturday, 07 December 2019 11:55

በአክቲቪስት ጀዋር የሚመራው ‹ቄሮ› በሽብርተኝነት እንዲፈረጅ አቤቱታ ቀረበ”

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(12 votes)

 በኢትዮጵያ የዘር ፍጅት ምልክቶችና የሰብዓዊ መብት ረገጣዎች መከሰታቸውን በመጠቆም፤ በአክቲቪስት ጀዋር መሃመድ የሚመራው ‹‹ቄሮ›› በሽብርተኝነት እንዲፈረጅ እነ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ለተባበሩት መንግስታት አቤቱታ ማቅረባቸው ተጠቆመ፡፡
በአሜሪካ ከደጋፊዎቻቸው ጋር ውይይት በማድረግ ላይ የሚገኙት ‹‹የአዲስ አበባ ባለደራ ም/ቤት›› ሰብሳቢ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋና አንጋፋው ምሁር ፕ/ር ጌታቸው ሀይሌ ባለፈው ረቡዕ ኒውዮርክ በሚገኘው የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጽ/ቤት አቤቱታውን በአካል ተገኝተው ማቅረባቸውን ጋዜጠኛ እስክንድር አስታውቋል፡፡
በአሜሪካ ከደጋፊዎቻቸው ጋር ባደረጓቸው ስብሰባዎች ከሕዝቡ የቀረቡላቸውን ጥያቄዎች መነሻ በማድረግ ጉዳዩን ለተባበሩት መንግስታት ሃላፊዎች ማስታወቃቸውን የገለፁት ጋዜጠኛ እስክንድር፤ በዋናነት በቅርቡ 86 ሰዎች የሞቱበትን ጥቃት መነሻ በማድረግ ስለተፈፀሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ማብራሪያ መስጠታቸው ተጠቁሟል፡፡
በአገሪቱ የዘር ማጥፋት ምልክቶች ስለመኖራቸውና ይህንንም በዋናነት እየፈፀመ ያለው በአክቲቪስት ጀዋር መሃመድ የሚመራው “የቄሮ ቡድን” መሆኑን ላነጋገሯቸው ከፍተኛ የመንግስታቱ ድርጅት ባለሥልጣናት መግለፃቸውን አመልክተዋል፡፡
“ኃላፊዎቹ አቤቱታችንን በሚገባ አድምጠዋል፤ ስለ ኢትዮጵያም ጥሩ መረጃ እንዳላቸው ተገንዝበናል” ብሏል ጋዜጠኛው:: ጠ/ሚኒስትሩ ስለተፈጠረውና ስለሞቱት ሰዎች የሰጡትን መግለጫም እንደማስረጃ ማቅረባቸውም ተገልጿል፡፡
ፕ/ር ጌታቸው ሃይሌ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ውስጥ በጥቃት ስለተፈናቀሉ ሰዎችና እየተፈፀመባቸው ስላለው የመብት ጥሰት ለመንግስታቱ ድርጅት ሃላፊዎች ማስረዳታቸውን ለመገናኛ ብዙኃን በሰጡት መግለጫ ጠቁመዋል::  ሕዝብን ከሕዝብ የማጋጨት ድርጊቶች በአገሪቱ ሃላፊነት በጎደላቸው አካላት እየተፈፀመ መሆኑንም በዝርዝር አስረድተናል ብለዋል - ፕ/ር ጌታቸው::
ሁለት አይነት የቄሮ ቡድን እንዳለ የሚገልፁት እነ ጋዜጠኛ እስክንድር፤ አንደኛው አምባገነናዊ አገዛዝን ለመቃወም የተሰባሰበና አላማውን አሳክቶ የተቀመጠ ሲሆን በሌላ በኩል በአቶ ጀዋር የሚመራ ጽንፈኛ የቄሮ ቡድን እንዳለ ለሃላፊዎቹ ማስረዳታቸውንም ጋዜጠኛ እስክንድር ብለዋል፡፡ ‹‹በሽብርተኝነት እንዲፈረጅ የተጠየቀውም ጥፋቶችን እያደረሰ ያለው በአቶ ጀዋር መሃመድ የሚመራው የቄሮ ቡድን ነው›› ብለዋል፡፡  በሌላ በኩል በአውሮፓ ሃገራት ከደጋፊዎቹ ጋር ስብሰባ ሲያደርግ የሰነበተው አክቲቪስት ጀዋር መሐመድ በበኩሉ፤ “እኔን ለመቃወም ሲባል የኦሮሞን ወጣት በሽብርተኝነት መፈረጅና መሳደብ አደገኛ አካሄድ ነው” ብሏል:: በኦሮሚያ ክልል ተፈጥሮ በነበረው ችግር የበለጠ የተጐዱት የኦሮሞ ተወላጆች እንደሆኑ የሚናገረው ጀዋር፤ በኦሮሚያ የተፈጠረው ችግር እሱ ካስተላለፈው ጥሪ ጋር የተያያዘ እንዳልነበር በመጠቆም የዶ/ር ዐቢይን መንግስት እንደግፋለን ብለው አደባባይ በወጡ ሃይሎች የተፈፀመ መሆኑን ለመገናኛ ብዙሃን መግለፁ አይዘነጋም፡፡

Read 12805 times