Saturday, 21 December 2019 11:52

የፀረ ጥላቻና የሀሰተኛ መረጃ ረቂቅ አዋጅ በድጋሚ እንዲጤን አለማቀፍ ተቋማት ጠየቁ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(5 votes)

        ፓርላማው በቅርቡ ያፀድቀዋል ተብሎ የሚጠበቀው የጥላቻ ንግግርና ሀሰተኛ መረጃን የሚመለከተው ረቂቅ ሕግ ያለ በቂ ጥናት የተዘጋጀ በመሆኑ በአገሪቱ የመናገር ነፃነትን ያፍናል የሚል ስጋት እንዳላቸው ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተቋማት ገልፀዋል፡፡
ረቂቅ አዋጁ በአገሪቱ ማህበራዊ ሚዲያን በመጠቀም የሚተላለፉ መልዕክቶችን ለመቆጣጠር የወጣ እንደመሆኑ፣ አንዳንድ በውስጡ የተካተቱ ድንጋጌዎች፣ የመንግሥት ባለሥልጣናት የዜጎችን የመናገር ነፃነት ለማፈን እንዲጠቀሙበት እድል የሚሰጥ ነው - ብሏል ሂውማን ራይትስ ዎች በወጣው ሪፖርት፡፡
ረቂቅ አዋጁ በዋናነት የጥላቻ ንግግርን የተረጎመበት መንገድ ከአለማቀፍ የመናገር ነፃነት ድንጋጌዎች ጋር በእጅጉ የሚቃረን ነው ያለው ተቋሙ፤ ድንጋጌው ለአሻሚ ትርጉሞችም የተጋለጠ ነው ብሏል፡፡
ባለሥልጣናት ሕጉን በፈለጉት አግባብ ተርጉመው ለማጥቂያነት ሊጠቀሙት ይችላሉ የሚል ስጋት እንዳለው በመግለጽም፤ አሻሚ ብያኔዎች ትርጉሞች፣ አገላለፆችና አንቀፆችን ያካተተው፤ ሕጉ በድጋሚ እንዲፈተሽ ጠይቋል፡፡
የኢትዮጵያ የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ የጥላቻ ንግግርና፣ ስድብን የሚከለክልበት ጠንካራ ድንጋጌ እንዳለው ጠቅሶ የተለየ ሕግ ማውጣት በራሱ አስፈላጊ አይደለም ብሏል - ተቋሙ፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትም፤ በረቂቅ ሕጉ ላይ ውይይት ሲያደርግ ተጨማሪ የመጨቆኛ መሳሪያ እንዳይሆን ማጤን እንዳለበት ያሳሰበው ሂዩማን ራይትስ ዎች፤ አቃቤ ሕጎች፣ ጠበቆች፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችና የሚዲያ ባለሙያዎች በጥልቀት ሊወያዩበት ይገባል ብሏል፡፡  በተመሳሳይ፤ የተባበሩት መንግሥታት የንግግር ነፃነት ከፍተኛ ባለሙያ ባለፈው ሳምንት ኢትዮጵያን በጎበኙበት ወቅት፤ ረቂቅ ሕጉ አለማቀፍ መስፈርቶችን የማያሟላና የመናገር ነፃነትን የሚገድብ ነው ሲሉ መተቸታቸው ተዘግቧል፡፡  

Read 922 times