Saturday, 11 January 2020 12:19

ወሲባዊ ጥቃት በወንዶች ላይ

Written by  ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
Rate this item
(1 Vote)


          በአለም አቀፍ ደረጃ ወደ 15/ሚሊዮን የሚሆኑ በእድሜያቸው ከ15-19 የሆኑ ታዳጊ  ልጃገረዶች በሕይወት ዘመናቸው አስገድዶ መድፈር እንደደረሰባቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
ምንም እንኩዋን በአለምአቀፍ ደረጃ መረጃዎች በትክክል ባይጠቁሙም ወንዶች ልጆችም የዚህ ሰቆቃ ሰለባ እንደሚሆኑ ተጠቁሞአል፡፡
ጾታዊ ጥቃት የሚባለው በብዙ አይነት መንገድ የሚገለጽ ጥቃት ሲሆን ይኼውም ስድብን፤ድብድብን፤ማንቋሸሽን …ወዘተ ባጠቃላይም በቀጥታ በአካል ላይ ከሚደርስ ጉዳት ጀምሮ እስከ ስነልቦና ጉዳት የሚደርሱ የተለያዩ ጥቃቶች አንዱ ጾታ በሌላው ጾታ ላይ ሲያደርስ የሚገለጽ በት ነው ጾታዊ ትንኮሳ ወይንም ጥቃት፡፡ ነገር ግን እነዚህ ሁሉ ድርጊቶች ወደከፋ ደረጃ ሲደርሱ ወሲባዊ ጥቃትን የሚያስከትሉበት አጋጣሚ ብዙ ነው፡፡ በእርግጥ ወሲባዊ ጥቃት በቀጥታ የሚነሳው ከሌሎቹ ጾታዊ ጥቃት ነው ሊባል ባይችልም አንዱ ጾታ በሌላው ላይ ካለምንም ፈቃደኝነት ጉልበትን ፤ኃይልን፤ ማታለልን፤ ማባበልን…ወዘተ ተጠቅሞ በሌላው ላይ ሲፈጽመው የሰብአዊ መብትን እንደመጣስ ከሚቆጠርበት ደረጃ ይደርሳል፡፡ በማንኛውም እድሜ ያሉ ሁሉም ህጻናት ጥቃቱ ሊደርስባቸው እንደሚችል የሚገመት ሲሆን በተለይም ታዳጊዎች ግን በተለይም ሴት ልጆች የጥቃቱ ሰለባ እንደሚሆኑ ይታመናል፡፡   
እንደ ዩኒሴፍ መረጃ በአለም አቀፍ ደረጃ የሚከተሉት መረጃዎች ተቀምጠዋል፡፡ www.unicef.org June 2016,  
38 በሚሆኑ መካከለኛ ገቢ ባላቸው ሀገሮች ወደ 17/ሚሊዮን የሚሆኑ ታዳጊ ሴቶች በልጅነት እድሜያቸው ተገዶ መደፈር እንደደረሰባቸው ሪፖርት አድርገዋል፡፡በአውሮፓ በ28 ሀገሮች ውስጥ ወደ 2.5 ሚሊዮን የሚሆኑ ታዳጊዎች ከአስራ አምስት አመት እድሜያቸው በፊት በተለያዩ መንገዶች ተገዶ መደፈር እንደደረሰባቸው የዩኒሴፍ ማስረጃ ያሳያል፡፡
በአለም አቀፍ ደረጃ ወደ 15 ሚሊዮን እድሜያቸው ከ15-19 አመት የሚሆኑ ታዳጊ ልጃገረዶች ተገዶ መደፈር የደረሰባቸው መሆኑ ሪፖርት ተደርጎአል፡፡  
በ20/ሀገሮች ከአስር ታዳጊ ልጃገረዶች ዘጠኙ እንደገለጹት ተገዶ የመደፈር ጥቃት ለመጀመሪያ ጊዜ የሚደርሰው በታዳጊነት እድሚያቸው ነው፡፡
ከ28 ሀገራት የተሰበሰበ መረጃ እንደሚሳየው ተገዶ መደፈር ከደረሰባቸው 10 ታዳጊ ልጃገረዶች ዘጠኙ ጥቃቱ የተፈጸመባቸው በሚያውቁዋቸውን በጣም ቅርብ በሆኑ ሰዎች ነው፡፡
ጉዋደንነት ወይንም በአንድ ክፍል መማር እና የቅርብ ጉዋደኝነት በታዳጊ ወንዶች ልጆች ላይ አስገድዶ መድፈር ለመፈጸም ምቹ ከሚባሉ ሁኔታዎች ውስጥ መሆኑን በተለያዩ ሀገራት የተደረጉ ጥናቶች ያሳያሉ፡፡
በ30 ሀገራት በተደረገው ጥናት እንደታየው ከሆነ ተገደው ከተደፈሩ ታዳጊ ልጃገረዶች ውስጥ 1በመቶ ያህሉ ብቻ የባለሙያ እርዳታ ለማግኘት የደረሰባቸውን ጥቃት ሪፖርት አድርገዋል፡፡
ከላይ ያነበባችሁት በታዳጊ ልጃገረዶች ላይ የሚደርሰውን አስገድዶ መድፈር የሚመለከት ሲሆን በመቀጠል በወንዶቹ ልጆች ላይ የሚፈጸመውን እናስነብባችሁዋለን፡፡
ወሲባዊ ጥቃት በወንዶች ላይ ፡-
በእርግጥ ወሲባዊ ጥቃት እድሜ እና ጾታ ሳለይ በማናቸውም ላይ እንደሚፈጸም የሚስተዋል አስከፊ ድርጊት ነው፡፡ ወንዶች እና ወንዶች ልጆች ላይ የሚደርሰው ወሲባዊ ጥቃትም ልክ በሴቶቹ ላይ እንደሚፈጸመው ከፍላጎት ውጪ በሆነ እና ኃይልን በመጠቀም የሚፈጸም ሲሆን ወሲባዊ ጥቃት ተፈጸመ ይባላል፡፡ ወሲባዊ ጥቃት የደረሰባቸው ወንዶች የሚደርስባቸው ጭንቀት ኃፍረትና በስሜት መጎዳት የሚደርስባቸው ሲሆን ከዚያም ባለፈ ወንድ ሆኖ በወሲብ መጠቃትን እንደ ከፍተኛ ነውርና እራስን በማህበራዊው አቋም ብዙ አድርጎ አለመቁጠር ወይንም ለእራስ ዝቅተኛ ግምት መስጠት የመሳሰሉት ሁኔታዎች ይስተዋሉባቸዋል፡፡
ወንዶች ወይንም ወንድ ልጆች(ታዳጊዎች)ወሲባዊ ጥቃት ሲደርስባቸው የሚያሳዩዋቸዋ ገጸ ባህርያት ተመሳሳይነት አላቸው፡፡ ወንዶች በመሆናቸውም በአብዛኛው መሆን የማይገባው ነገር በመፈጸሙና የወንድነት ክብራቸው እንደተነካ ስለሚያምኑ በሕይወታቸው ከገጠሙዋቸው ነገሮች ሁሉ መልስ ወይንም መፍትሔ ሊያገኙለት የማይችሉት አስቸጋሪ ነገር ይሆንባቸዋል፡፡
አንዳንድ ወንዶች በታዳጊነታቸው ጊዜ ተገዶ መደፈር ከደረሰባቸው እፍረት እና ያንን ጉዳት ያደረሰባቸውን ሰው ለመበቀል የሚያስችል አቅም አለኝ በሚል በራስ ያለመተማመን ስሜት ውስጥ ይወድቃሉ፡፡ ብዙ ወንዶች በድርጊቱ የሚደነቁና የደፈሩዋቸው ወንዶች እንዴት ከስሜት ውጭ በሆነ መንገድ በእነሱ ላይ ጉልበታቸውን ተጠቅመው ወሲብ እንደፈጸሙ …ወዘተ የመሳሰሉትን ድርጊቶች በሕይወት ዘመናቸው አምነው ሊቀበሉት የማይችሉት እና ምን ማለት እንደሆነ ትርጉም ያጡለታል፡፡ ለዚህ ድርጊትም የስነልቡ ምላሽ ….አንተ አልተጠየቅህም፤ፈቃደኛ አልነበርክም፤አልተጋበዝክም ወይንም አልረካህበትም የሚል ነው፡፡ ስለዚህም ምንም አይነት ነገር ከአንተ ፈቃደኝነት ውጭ ከተፈጸመብህ የእራስህ ጥፋት አድርገህ እንዳትቆጥረው እና ተገቢውን ምላሽ በማግኘት ረገድ ብቸኛው ነኝ ብለህ እንዳታስብ ይላል የባለሙያዎች ማብራሪያ፡፡
ወንዶች በታዳጊነት ዘመናቸው ተገዶ መደፈር ከደረሰባቸው በእድሜያቸው ከፍ ካሉ በሁዋላ መደፈር ከሚደርስባቸው የተለየ ባህርይ ያሳይሉ:: በተከታይነት የተዘረዘሩት ትልልቅ ወንዶችና ታዳጊዎች ተገዶ መደፈር ከደረሰባቸው በሁዋላ ከሚታዩባቸው ተመሳሳይ ባህርያት መካከል ናቸው:: በእርግጥ ባህርያቶቹ በሌሎችም ሰዎች ሊታዩ ይችላሉ፡፡
ግራ መጋባት፤ ድብርት፤ ጭንቀት፤ የአመጋገብ ስርአት አለመኖር…ወዘተ፤
ተገዶ መደፈሩን የሚያስታውስ ቦታም ሆነ ሰዎችን ማስወገድ፤
ስለ ወሲባዊ ድርጊት ጥያቄዎችን መጠየቅ ወይንም በጉዳዩ ላይ ትኩረት ማድረግ፤
መጥፎ ነገር እንደተፈጸመ አድርጎ ማሰብና ፍርሀትን ማሳደር እንዲሁም የወደፊት ሕይወት አጭር ናት ብሎ ተስፋ መቁረጥ፤
ከሰው በታች ነኝ ብሎ ማሰብ ወይንም ለወደፊቱም በራሴ ገላ ላይ ማዘዝ የማልችል ነኝ ብሎ ማሰብ፤
እራስን ለማዝናናት አለመፈለግ እና በበቂ ሁኔታ እንቅልፍ አለመተኛት፤
ተገዶ የመደፈርን ድርጊት ባለማስቆም ምክንያት ለእራስ እፍረት መሰማት እና እራስን ጥፋተኛ በማድረግ መውቀስ፤
ከማንም ጋር ግንኙነት ላለመፍጠር ወይንም ጉዋደኛ ላለማፍራት መሞከር እና እራስን የማግለል ድርጊት፤
ፍትሕ አገኛለሁ ብሎ ካለማመን ወይንም ከመፍራት የተነሳ ድርጊቱ መፈጸሙን ለሚመለከተው ማለትም ለቤተሰብ…ለጤና ወይም ለፍትሕ ተቋም ግልጽ አለማድረግ ስህተት ነው ብሎ በማያቋርጥ ሁኔታ መጨነቅ፤ የመሳሰሉት ይታዩባቸዋል፡፡
ከላይ በተገለጸው መንገድ ተገዶ በመደፈር ምክንያት ስሜታቸው የተጎዳ ወንዶችን ለመርዳት በሚከተሉት መንገዶች መቅረብ ጠቃሚ ነው፡፡
ማዳመጥ፡፡ ብዙ ሰዎች ችግር እንደደረሰባቸው ካመኑ ሌላ ሰው ስለ ችግሩ ይገባዋል ወይንም ሊያዳምጠኝ ይችላል ብለው አያምኑም፡፡ ስለዚህ በእርጋታ ማዳመጥ ይገባል፡፡
ሀሳባቸውን ባቀረቡበት መንገድ መቀበልና ተናጋሪውን አምንሀለሁ ወይንም እንደገለጽከው ችግሩ ሰፊ ነው ማለት አይጠቅማል፡፡ ጉዳቱ የደረሰበት ሰው የሚናገረውን ነገር ማቅለል ወይንም ችግሩ እኮ ከባድ አይደለም በማለት ለማባበል መሞከር ተገቢ አይደለም፡፡
እኔ እዚህ ያለሁት አንተን ለማዳመጥ ነው ወይንም የደረሰብህን ችግር መፍትሔ ለመስጠት እሰራለሁ …ወዘተ የመሳሰሉ ነገሮችን መንገር፡፡
ስለጉዳቱ አፈጻጸም ዝርዝር ነገሮችን መጠየቅ አይገባም፡፡

Read 13901 times