ከጥቂት ሳምንታት በፊት በዋልታ ቴሌቪዥን ሕጋዊ ዌብሳይት ላይ በወጣውና ከትግራይ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል ጋር በተያያዘው ዜና ሳቢያ የዋልታ ቴሌቪዥን አራት ጋዜጠኞችና ሦስት ቴክኒሺያኖች ታሰሩ፡፡ በቁጥጥር ስር የዋሉት ጋዜጠኞችና ቴክኒሺያኖች የት እንደታሰሩ እንደማይታወቅ ምንጮች ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
እንደ ምንጮቻችን ገለጻ፤ ከትናንት በስቲያ በዋልታ ቴሌቪዥን ግቢ ውስጥ የተገኙት የደህንነት አባላት ናቸው የተባሉት ግለሰቦች ከዚሁ ዜና ጋር በተያያዘ ለጊዜው ከሥራቸው ታግደው የነበሩትን አራት ጋዜጠኞች በቴሌቪዥን ጣቢያው ሃላፊ የስልክ ጥሪ ወደ ግቢው እንዲመጡ ካደረጉ በኋላ አራቱን ጋዜጠኞችና ሦስቱን የቴሌቪዥን ቴክኒሺያኖች በያዙት መኪና ይዘዋቸው ሄደዋል፡፡ ጋዜጠኞቹ ወደ 3ኛ ፖሊስ ጣቢያ እንደሚወሰዱ የተነገረ ቢሆንም በተባለው ቦታ የቴሌቪዥን ጣቢያውን ሠራተኞች ለማግኘት እንዳልተቻለ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ሁኔታው የቴሌቪዥን ጣቢያውን ጋዜጠኞችና ሰራተኞች ስሜት በእጅጉ የጎዳ መሆኑን የጠቆሙት ምንጮቻችን፤ በስልክ ተጠርተው የተወሰዱት የአራቱ ጋዜጠኞችና የሶስቱ ቴክኒሺያኖች ደህንነት በእጅጉ እንደሚያሰጋቸው ገልፀዋል፡፡